ፈልግ

የሱዳን ህዝባዊ የእርዳታ ትስስር ረሃብን ለመከላከል ጥረት እያደረገ ነው የሱዳን ህዝባዊ የእርዳታ ትስስር ረሃብን ለመከላከል ጥረት እያደረገ ነው  

በዓለም የምግብ እና እርሻ ድርጅት የቅድስት መንበር ቋሚ ታዛቢ “ረሃብን ለማጥፋት ሰላም አስፈላጊ ነው" ማለታቸው ተነገረ

በመካከለኛው ምሥራቅ እየተካሄደ በሚገኘው ጦርነት ምክንያት የደረሰው ሥርዓታዊ ቀውስን አስመልክተው በዓለም የምግብ እና እርሻ ድርጅት የቅድስት መንበር ቋሚ ታዛቢ የሆኑት ሊቀ ጳጳስ ፈርናንዶ ቺካ ገበያን ለማረጋጋት እና ለችግር ተጋላጭ የሆኑ ዜጎችን ለመጠበቅ አፋጣኝ እርምጃ እንዲወሰድ በማሳሰብ፥ “ዘላቂ ልማትን ለማረጋገጥ ለዲፕሎማሲ ቅድሚያ መስጠት” እንደሚገባ ገልጸዋል።

  አቅራቢ ዘላለም ኃይሉ ፥ አዲስ አበባ

ቅድስት መንበር በመካከለኛው ምስራቅ እና በአፍሪካ ህዝቦች ላይ እየደረሱ የሚገኙትን በርካታ ሰብዓዊ ቀውሶች እና በአግሮ የምግብ ማምረቻ ስርዓቶች ላይ ከፍተኛ ተጽእኖ እያደረሰ በመምጣቱ ያላትን ጥልቅ ስጋት የገለጸች ሲህን፥ በቀጠናዎቹ የተከሰቱት ግጭቶች እና ከባድ የአየር ንብረት ለውጥ አደጋዎች ከጊዜ ወደ ጊዜ ቁጥራቸው እየጨመረ የመጣ ሰዎችን ለድህነት፣ ለረሃብ እና ለምግብ እጦት እየዳረገ መምጣቱን አሳስባለች።

በዓለም የምግብ እና እርሻ ድርጅት፣ በዓለም አቀፍ የግብርና ልማት ፈንድ ድርጅት (IFAD)፣ እና በዓለም የምግብ ፕሮግራም (WFP) የቅድስት መንበር ቋሚ ታዛቢ የሆኑት ሊቀ ጳጳስ ፈርናንዶ ቺካ አሬላኖ ይሄንን አሳሳቢ ሁኔታ የገለጹት በመካከለኛው ምሥራቅ 38ኛው ክልላዊ ጉባኤ (NERC) በተካሄደበት ወቅት ሲሆን፥ በጉባኤው ወቅት ከተነሱት ዋና ዋና ርዕሰ ጉዳዮች መካከል አንዱ የነበረው በመካሄድ ላይ ባለው ግጭት ምክንያት በአግሮ- የምግብ ማምረቻ ሥርዓት ላይ ለሚከሰቱት ስርዓታዊ ቀውሶች ምላሽ ለመስጠት ስልታዊ እርምጃዎች መወሰድ አለባቸው የሚል እንደነበር ተገልጿል።

የተቀናጀ ፖለቲካዊ ምላሽ
ሊቀ ጳጳስ ቺካ እንደገለጹት ‘የኃይል እና የማዳበሪያ ወጪዎች እየጨመረ ከመጣው የአቅርቦት ሰንሰለት ጋር ተዳምሮ፥ በተለይም ከውጭ በሚገቡ ምርቶች ላይ የተመሰረቱ ተጋላጭ በሆኑ ሀገራት የምርት ወጪን እያሳደገው እና የምግብ ዋጋ ንረቱን እያባባሰ’ መምጣቱን ጠቁመዋል።

የቅድስት መንበር ቋሚ ታዛቢው “በአሁኑ ወቅት በመካከለኛው ምሥራቅ እየተባባሰ የመጣው ግጭት ከድንበር ባለፈ መዘዝ እንደሚኖረው እና በዓለም አቀፍ ደረጃ በተለይም ለችግር ተጋላጭ በሆኑት ሕዝቦች ላይ ረሃብን የበለጠ እንደሚያባብስ አስረድተዋል።

የኃይል እና የምግብ ዋስትናን ማረጋገጥ
ጉባኤው “በተለይ በአካባቢው የሚፈጠሩ ግጭቶች ወደ ሰፊ ኢኮኖሚያዊ እና ሰብዓዊ ቀውሶች እንዳይሸጋገሩ መከላከልን ይመለከታል” ያሉት ሊቀ ጳጳሱ፥ በዚህ አውድ ውስጥ ዓለም አቀፍ የኢነርጂ እና የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ እና የአቅርቦት ሰንሰለትን ለማረጋጋት አፋጣኝ እርምጃዎች መወሰድ እንዳለባቸው፣ እንዲሁም ዘላቂ የሆነ ብሔራዊ የግብርና አሰራርን፣ ታዳሽ ኃይል እና መዋቅራዊ ማስተካከያ ላይ ያተኮሩ የረዥም ጊዜ ስልቶች መወሰድ እንዳለባቸው አመላክተዋል።

የርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳቱ ጥሪ
ቋሚ ታዛቢው በጉባዔው ላይ ለተገኙት ተሳታፊዎች ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ሊዮ አሥራ አራተኛ ድህነትን እና የምግብ ዋስትና እጦትን የሚያባብሱ በርካታ የአለመረጋጋት ምክንያቶችን ፊት ለፊት ለመጋፈጥ እንዲቻል በተደጋጋሚ ሰላም እንዲሰፍን ሲመክሩ እንደነበር አስታውሰዋል።

በቅን ልቦና ላይ የተመሰረተ ውይይት እና የእያንዳንዱን ሰው ክብር የጠበቀ የሰላም መንገዶችን ለመፈለግ የመለያየት እና በጠላትነት ስሜት የመተያየት አዝማሚያ ማብቃት እንዳለበት የጠቆሙት ሊቀ ጳጳሱ፥ ተግዳሮቱ ምንም እንኳን ንፁሀን ቢሆኑም በአሳዛኝ ሁኔታ ሌሎች በሚያነሱት ግጭቶች ሰለባ የሚሆኑትን ህዝቦች ስቃይ ማቃለል እንደሆነም ጭምር አስረድተዋል።

ሊቀ ጳጳስ ቺካ አሬላኖ በመቀጠልም በጦርነት እና በግጭት ውስጥ በሚገኙ በርካታ የዓለማችን ክልሎች ውስጥ ያለውን አስከፊ ሁኔታ ቅድስት መንበር በቅርበት እየተከታተለች መሆኑን ያረጋገጡ ሲሆን፥ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ሊዮ አስራ አራተኛ አጽንኦት ሰጥተው እንደገለፁት በእነዚህ ጦርነቶች ምክንያት የሚደርሰው ሞትና ስቃይ በሰው ልጆች ሁሉ ላይ የደረሰ ውርደት እና ወደ እግዚአብሔር የሚቀርብ ጩኸት እንደሆነ ገልጸው፥ “የጦር መሣሪያዎች ድምፅ እንዲቆም እና የሕዝብ ድምፅ የሚሰማበት ቦታ እንዲፈጠር ሰላምን ማስፈን የሁሉም ዲፕሎማሲያዊ ተግባራት ማዕከል መሆን አለበት” ብለዋል።

በመፍትሄ ሃሳቦች ዙሪያ መደራደር
ሊቀ ጳጳስ ቺካ አሬላኖ አጽንኦት ሰጥተው እንደተናገሩት ‘ለተከሰቱት ግጭቶች በድርድር መፍትሄ በቅርቡ እንደሚገኝ’ ያላቸውን ተስፋ ገልጸው፥ የቅድስት መንበር ልዑካን የዚህ ክልላዊ ጉባኤ ሥራ ዓለም አቀፍ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ የሚረዱ መርሆችንና ድንጋጌዎችን ለማፅደቅ እና ሰላምን ለማስፈን የሚረዱ መርሆች እና ድንጋጌዎችን ለማፅደቅ የበኩላቸውን አስተዋጽኦ እንደሚያበረክቱ በመተማመን፥ ትክክለኛ የሆነ ዘላቂ ልማት ለማረጋገጥ እና በዓለም ላይ ረሃብን ለማጥፋት አስፈላጊ የሆኑ መፍትሄዎችን መፈለግ እንደሆነ በመግልጽ አጠቃልዋል።

23 Apr 2026, 13:48