ፈልግ

የቫቲካን ራዲዮ እ.አ.አ 2931 ዓ.ም ሲመረቅ የምያሳይ ምስል የቫቲካን ራዲዮ እ.አ.አ 2931 ዓ.ም ሲመረቅ የምያሳይ ምስል  ርዕሰ አንቀጽ

መልካም ልደት! የቫቲካን ሬዲዮ፡- ጳጳሳቱን ማገልገል የጀመረበት 95 ዓመት እየተከበረ ይገኛል።

ማርኮኒ ጉሌልሞ እ.አ.አ በ1931 ዓ.ም የመጀመሪያውን የሬዲዮ ስርጭት ከጀመረበት እስከ ዛሬው ዲጂታል እና አርቴፊሻል ኢንተለጀንስ ዘመን ድረስ፣ የቫቲካን ሬዲዮ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሱን፣ የቅዱስ ወንጌል ስርጭትን በዓለም ዙሪያ ላሉ ማህበረሰቦች ለባለፉት 95 ዓመታትን በማስተላለፍ አገልግሏል።

የዚህ ዝግጅት አቅራቢ መብራቱ ኃ/ጊዮርጊስ-ቫቲካን

ከ95 ዓመታት በኋላ የቫቲካን ሬዲዮ ድምፅ በዓለም ዙሪያ እየተዘዋወረ የወንጌልን፣ የተስፋን እና የቅዱስ ጴጥሮስ ተተኪ ቃል በየቦታው ይዞ መሄዱን ማንጸባረቁ በጣም ልብ የሚነካ ነው። እያንዳንዱን ድንበር እና ርቀት አቋርጦ በመሄድ ለሁሉም የሕብረተሰብ ክፍሎች የሰላም እና የተስፋ መልእክት በማስተላለፍ ላይ ይገኛል።

ዛሬ፣ ሀሳባችን እ.አ.አ ወደ የካቲት 12 ቀን 1931 ዓ.ም. ይመለሳል፤ የመጀመሪያው ድምፅ "በስታቲዮ ሬዲዮፎኒካ ቫቲካና" ማይክሮፎኖች በኩል የሚናገረው የሳይንቲስቱ ጉሌልሞ ማርኮኒ ነበር። ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፒየስ 11ኛ ማርኮኒን ይህን አስደናቂ የመገናኛ መሣሪያ የመንደፍና የመገንባት ሥራ አደራ ሰጥተውት ነበር።

የሬዲዮ አባት ለመጀመሪያ ጊዜ የጳጳሱ ድምፅ “በምድር ላይ በሙሉ በአንድ ጊዜ ሊታወቅ” እንደሚችል አስታውቀዋል፤ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳቱም በላቲን ቋንቋ ሲናገሩ በቫቲካን ታሪክ ውስጥ የመጀመሪያውን የሬዲዮ መልእክት “ለሁሉም ሕዝቦችና ለእያንዳንዱ ፍጥረት” በታላቅ ውበት ልከዋል። ከዚያም ከቤትሆቨን ሲምፎኒ የተወሰዱ ዜማዎች ተሰራጭተው ነበር።

የርዕሰ ሊቃነ ጳጳሱ ግንዛቤ በሰው ልጅ ግንኙነት አገልግሎት እና በቤተክርስቲያኗ ተልዕኮ ላይ በተቀመጠው የቴክኖሎጂ እድሎች ላይ ጥልቅ እምነት እንዳለው አረጋግጧል። ተራ ቴክኒካዊ ሙከራ አልነበረም፣ ነገር ግን ትክክለኛ የአንድ መንፈሳዊ እረኛ ምርጫ ነበር፣ የሰዎችን ልብ ለመንካት በወቅቱ እጅግ የላቀውን መንገድ መጠቀም እንደሆነም ተገልጿል።

ከዚያን ጊዜ ጀምሮ የቫቲካን ሬዲዮ በታሪክ ውስጥ አልፏል፣ በጦርነቶችና በሰላም ስምምነቶች፣ በድህነትና በእርዳታ፣ በጥፋትና በመልሶ ግንባታ፣ በማግለልና በአቀባበል፣ በማህበራዊ፣ በፖለቲካዊና በቴክኖሎጂ ለውጦች፣ እና ሁልጊዜም የክርስትናን አዋጅ፣ የተስፋ ብርሃን እና ክስተቶችን በካቶሊክ ማህበራዊ ትምህርት መነፅር በመተርጎም ሲያከናውን ቆይቷል።

እስከዛሬ ድረስ የቫቲካን ሬዲዮ ዘጠኝ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳትን አገልግሏል። በሁለተኛው የዓለም ጦርነት ወቅት በሺዎች የሚቆጠሩ የጠፉ ሰዎችን እንደገና ለማሰባሰብ ረድቷል። በአምባገነናዊ ሥርዓቶች ጨለማ ዓመታት ውስጥ እንደ መብራት ሆኖ አገልግሏል። የሁለተኛውን የቫቲካን ጉባኤ፣ የኢዩቤሊዩን፣ የዓለም አቀፋዊቷ ቤተክርስቲያን ተግዳሮቶች እና በቅርብ ጊዜ በዩክሬን፣ በመካከለኛው ምስራቅ፣ በኮንጎ፣ በምያንማር፣ በየመን እና በሶሪያ የተከሰቱትን ጨምሮ በርካታ፣ በጣም ብዙ ግጭቶችን ዘርዝሯል፣ ዘግቧል። የጸሎት፣ የመረጃ እና የተስፋ መንገድ ሆኖ ቆይቷል፣ እናም ሆኖም ቀጥሏል።

ብዝሃ-ባህልነት ዓለምን ለማንበብ ልዩ መለያ ምልክት እና ውድ ቁልፍ ነው። ዛሬ፣ ለጳጳሳዊው ብሮድካስት የሚሰሩት ከስልሳ ዘጠኝ አገሮች የተውጣጡ ሰዎች በመሥራት ላይ ይገኛሉ፣ እናም በ34 ቋንቋዎች በሚዘጋጁ የኤዲቶሪያል ቢሮዎች፣ እንዲሁም በመልቲሚዲያ አማካኝነት፣ የዓለምን መልካምድራዊ እና የህልውና ዳርቻዎች እንደርሳለን፣ ከዋና ዋና የሚዲያ ወረዳዎች ርቀው ላሉ ማህበረሰቦች ድምጽ እንሰጣለን እና የአካባቢ አብያተ ክርስቲያናት ሕይወትን እናከብራለን፣ እንዘግባለን። በብዙ አገሮች፣ የጳጳሱ ሬዲዮ ለአስርተ ዓመታት፣ እና በአንዳንድ ቦታዎች ለክርስቲያን ማህበረሰቦች እና ከዚያም በላይ ለሆኑ ማህበረሰቦች ምስጢራዊ ግን መሠረታዊ መገኘት አለው።

በቅርብ ዓመታት፣ የጳጳሱ ሬዲዮ በቀድሞ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንችስኮስ የተጀመረውን ሰፊ ​​የመገናኛ ብዙሃን ማሻሻያ ውስጥ ጥልቅ ለውጥ አድርጓል። በቫቲካን የኮሚውኒኬሽን ጽ/ቤት መመስረት እና የተለያዩ የሚዲያ አካላትን ወደ አንድነት እና የተቀናጀ ስርዓት ማዋሃድ ድርጅታዊ፣ ሙያዊ እና ባህላዊ ለውጦችን ጠይቋል። ቀላል ጉዞ አልነበረም እና አሁንም ቀጥሏል፣ ነገር ግን መሳሪያዎች እና ቋንቋዎች በፍጥነት በሚለዋወጡበት በየጊዜው በሚለዋወጡ አውድ ውስጥ ለቅዱስ አባታችን እና ለእውነት አገልግሎት ባለን ተልእኮ ግልጽ ግንዛቤ አማካኝነት የሚቀጥል ነው። በዚህ መንገድ፣ ሥራችንን በተደጋጋሚ ተቀብለው የአንድነት፣ የእውነትን አገልግሎት እና የእግዚአብሔርን ሕዝብ ሕይወት “ትጥቅ የፈተና ትጥቅ በምያስፈታ የኮሚውኒኬሽን ግንኙነት” አስፈላጊነትን ሲያስታውሱ በነበሩት የርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ሊዮ ቃላት ተበረታተናል፤ እነዚህም ሰዎች የበለጠ ወንድማማችነትን፣ ደጋፊ፣ እንግዳ ተቀባይ እና ሰላማዊ ማህበረሰብ ለመገንባት አስተዋጽኦ ማድረግ የሚችል ግንኙነት አማካኝነት የእግዚአብሔርን ሕዝብ ሕይወት ማጀብ ናቸው።

ቫቲካን ሬዲዮ፣ የቫቲካን ዜና ዲጂታል ሥርጭት በ56 ቋንቋዎች በጽሑፍ፣ በግንባር እና በምልክት ቋንቋዎች ታዳሚዎችን በሬዲዮ ሞገዶች፣ በሳተላይት፣ በቀጥታ ስርጭት፣ በፖድካስት፣ በማህበራዊ ሚዲያ፣ በቪዲዮ እና በዲጂታል መድረኮች ዝግጅቱን ያስተላልፋል።

የቫቲካን ሬዲዮ ዘጠና አምስተኛ ዓመት የሚከበረው በአርቴፊሻል ኢንተለጀንስ ዘመን ሲሆን የሚዲያ እና የመገናኛ ዓለምን በጥልቀት እየለወጠ ነው። AI ያለምንም ጥርጥር ጠቃሚ እርዳታ፣ ጠቃሚ መሳሪያ ነው፣ ነገር ግን ስልተ ቀመሮች የሰውን ነገር መተካት አይችሉም እና ሊተኩ አይገባም፤ አስተሳሰብ፣ ፈጠራ እና ፍርድ ሊሰጥ የምችል ክህሎት የላቸውም።

እ.አ.አ ከ2012 ዓ.ም ጀምሮ፣ የእኛ ክብረ በዓል በየካቲት 13 በዩኔስኮ ከተቋቋመው የዓለም የሬዲዮ ቀን ጋር ተገጣጠመ፣ ይህም በዚህ ዓመት “AI መሳሪያ ነው፣ ድምጽ አይደለም” በሚለው ጭብጥ እንዲከበር ተወስኗል። ይህ አገላለጽ ቅዱስ አባታችን እ.አ.አ የ2026ቱን የዓለም የመገናኛ ቀን አስመልክቶ ከሰጡት መልእክት ጋር በጥልቅ ይስማማል፤ ይህም የግል ኃላፊነትን፣ ማስተዋልን እና የማይተካ የሰው ልጅ የመግባቢያ ዋጋን ያስታውሳል።

ቫቲካን ሬዲዮ ሁልጊዜ ለቴክኖሎጂ ድንበሮች ትኩረት ይሰጣል፤ አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ የሚያቀርባቸውን እድሎች በእርግጥ ይዳስሳል፤ ነገር ግን ሬዲዮ በሰዎች መካከል የሚደረግ ግንኙነት ነው የሚለውን እምነት፣ ከፊት፣ ከህሊና እና ከኃላፊነት የሚመጣ ቃል ነው የሚለውን እምነት ፈጽሞ አይዘነጋም።

በዚህ መልኩ፣ የጳጳሱ ሬዲዮ ቴክኖሎጂ ከማርኮኒ አመጣጥ ጀምሮ ለሰው ልጅ አገልግሎት እንጂ ለሌላ ጥቅም እንዳልሆነ መመስከሩን ቀጥሏል።

ዛሬም እ.አ.አ እንደ 1931 ዓ.ም፣ የጳጳሱ ሬዲዮ ተልዕኮውን ቀጥሏል፡ የወንጌልን መልእክት፣ የጳጳሱን ድምፅ እና የጳጳሱን አስተምህሮ በመላው ዓለም ማሰራጨት፣ ማህበረሰቦችን ማግኘት፣ ማዳመጥ እና ማገልገል ቀጥሏል።

መልካም ልደት፣ ለቫቲካን ሬዲዮ።

 

12 Feb 2026, 14:43