“ከርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ጋር አብረን እንጸልይ!” የሚል የጸሎት ተነሳሽነት ይፋ መደረጉ ተገለጸ
የዚህ ዝግጅት አቅራቢ ዮሐንስ መኰንን - ቫቲካን
“ከርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ጋር አብረን እንጸልይ!” በሚል ቫቲካን ውስጥ ከሚገኘው ቅዱስ ፔሬግሪን ጸሎት ቤት ወደ ዓለም በሙሉ የሚሰራጨው የጸሎት መርሃ ግብር ምእመናን ከርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ሊዮ 14ኛ ጋር በጸሎት እንዲተባበሩ የሚጋብዝ እንደሆነ ታውቋል።
ረቡዕ ታኅሳስ 29/2018 ዓ. ም. ይፋ የተደረገው የጸሎት ተነሳሽነቱ ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ሊዮ 14ኛ እንደ ጎርጎሮሳውያኑ በ 2026 አዲስ ዓመት የሚያጋሩት የመጀመሪያው የጸሎት ሃሳብ ከመለቀቁ ጥቂት ቀደም ብሎ ሲሆን፥ በእንግሊዝኛ፣ በጣሊያንኛ እና በስፓኒሽ ቋንቋዎች በተዘጋጁ የቪዲዮ ቅንብሮች ይፋ መሆኑ ታውቋል።
ጸሎት እንደ ተስፋ ምንጭ
ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ሊዮ 14ኛ፥ “በእግዚአብሔር ቃል በመታገዝ መጸለይ” በሚል ሃሳብ ለጥር ወር ባዘጋጁት የጸሎት ሃሳባቸው ምእመናን ጸሎትን እንደ ተስፋ ምንጭ አድርገው በድጋሚ እንዲገነዘቡት ጥሪ አቅርበዋል። የጸሎት ተነሳሽነቱ በንግግር ሳይሆን ሁካታ እና መዘናጋት በበዛበት ዘመን በጸጥታ እና በአስተንትኖ መካሄድ እንደሚገባ አሳስበዋል።
የተረጋጋ የጸሎት ጊዜ
የቅድስት መንበር መገናኛዎች ጽሕፈት ቤት ተጠሪ አቶ ፓውሎ ሩፊኒ፥ ተነሳሽነቱ የርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ቅርብ እና ሁሉ አቀፍ ጸሎትን አዲስ እና ንቁ በሆነ መንግድ እንደሚያቀርብ፥ ይህም አንድነት እና ኅብረት የሚታይበት ምልክት ሆኖ እንደሚያገለግል ገልጸው፥ “ከእያንዳንዱ ሰው ልብ ጀምሮ በዲጂታል ዓለም እና በዕለት ተዕለት ሕይወት ተጨባጭ እውነታዎች ውስጥ ለሚሊዮኖች የመሰብሰቢያ ቦታ ይሆናል” ሲሉ አስረድተዋል።
ይህ ሃሳብ ለጸሎት የተመቻቸ ሥፍራን እና የተረጋጋ ጊዜን በመፍጠር የዘመናዊውን ሕይወት ጥድፊያ እንደሚያስቀር አቶ ሩፊኒ አብራርተው፥ በመለያየት፣ በጦርነት እና በዓመፅ በተሞላ ዓለም ውስጥ እውነተኛ ግንኙነት የሚቻል መሆኑን ተናግረው፥ ጸሎት የተበታተኑትን ወደ አንድነት የመመለስ ኃይል እንዳለው አፅንዖት ሰጥተዋል።
ወርሃዊ የጸሎት ሃሳቦችን እና ዓለም አቀፍ ስጋቶች
ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ሊዮ 14ኛ በአዲሱ የጎርጎሮሳውያን 2026 ዓ. ም. ቤተ ክርስቲያን በየወሩ በአንድ የተወሰነ ርዕሠ ጉዳይ ዙሪያ እንደ ሰላም እና የጦር መሣሪያ ማስፈታት፣ ዓለም አቀፍ ተግዳሮቶች እና በቤተ ክርስቲያን ሕይወት ውስጥ ያሉ ጉዳዮችን ጨምሮ ለስብከተ ወንጌል አገልግሎት ስኬታማነት እንድትጸልይ አደራ ብለዋል።
ይህ ተነሳሽነት ከአሥር ዓመታት በፊት በነፍስሔር ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንችስኮስ የተጀመረ እና በዓለም ዙሪያ ከ260 ሚሊዮን ጊዜ በላይ ዕይታ ያለው የርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት የቪዲዮ ውርስ እንዲቀጥ የሚያደርግ መሆኑ ታውቋል።
ልዩ “ኔትወርክ” ዓይነት መገንባት
ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ሊዮ 14ኛ በዲጂታሉ ዘመን “የመገናኛ መረቦችን መጠገን ያስፈልጋል” በማለት ያቀረቡትን ግብዣ ያስታወሱት አቶ ፓውሎ ሩፊኒ፥ ይህም በምኞት ወይም በጉልበት ሳይሆን በእውነት አስፈላጊ የሆነውን እንደገና ማግኘት እንደ ሆነ ገልጸው፥ በገንዘብ ማግኛነት የሚታወቁ አውታረ መረቦችን ለጸሎት አውታረ መረብነት መጠቀም እንግዳ ነገር ሊመስል ቢችልም በኅብረት መጸለይ ኅብረት የሚገነባበት መንገድ እንደሆነ እና በዓለማዊ ማኅበረሰቦች ውስጥ ለጥልቅ መንፈሳዊነት ምላሽ እንደሚሰጥ አስረድተዋል።
ለጋራ ጸሎት የተከፈተ በር
የርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ዓለም አቀፍ የጸሎት “ኔትወርክ” ዳይሬክተር አባ ክሪስቶባል ፎኔስ “ከርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ጋር አብረን እንጸልይ” የሚለው ተነሳሽነት ከሲኖዶሳዊነት እይታ አንጻር ማንኛውም ሰው በየትኛውም ቦታ ሆኖ የርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳትን ወርሃዊ የጸሎት ሃሳብ እንዲቀላቀል ነጻ ግብዣን እንደሚያቀርብ አስረድተዋል። ይህ ዓለም አቀፍ ገጽታ ያለው እና ከኢንዶኔዥያ እና ከኮት ዲቩዋር በተገኙ የቪዲዮ ምስክርነቶች ላይ የሚያተኩረው ቅንብሩ ጸሎትን በባህሎች እና በሕዝቦች መካከል እንደ ድልድይ አድርጎ እንደሚያቀርብ ታውቋል።
በመጨረሻም የቅድስት መንበር መገናኛዎች ጽሕፈት ቤት ተጠሪ አቶ ፓውሎ ሩፊኒ ከጋዜጠኞች ለቀረበላቸው ጥያቄ በሰጡት ምላሽ፥ ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ሊዮ 14ኛ ተነሳሽነቱን እንደደገፉት እና ለሚቀጥሉት ወራት የሚሆኑ የቪዲዮ ምስሎችን እንደተቀረጹ ተናግረው፥ በማኅበራዊ ሚዲያ አማካይነት ባስተላለፉት አጭር መልዕክትም ሰዎች ማለቂያ ከሌለው የማኅበራዊ ሚዲያ መስኮቶች ርቀው ለጸሎት ቦታ እንዲሰጡ ማሳሰባቸውን በማስታወስ፥ “ይህምትኩረትን ያለማቋረጥ በሚከፋፍሉ ነገሮች የተሰቃዩ ልቦች ከእግዚአብሔር ቃል አዲስ ሕይወት እንዲያገኙ ያስችለዋል” ብለዋል።