የቅድስት መንበር ዋና ጸሐፊ ብፁዕ ካርዲናል ፒየትሮ ፓሮሊን፥የ2025 ዓ. ም. (እአአ) ሪፖርት በማስመልከት ለጉባኤው ንግግር ሲያደርጉ የቅድስት መንበር ዋና ጸሐፊ ብፁዕ ካርዲናል ፒየትሮ ፓሮሊን፥የ2025 ዓ. ም. (እአአ) ሪፖርት በማስመልከት ለጉባኤው ንግግር ሲያደርጉ 

ብፁዕ ካርዲናል ፓሮሊን በሁሉም አካባቢዎች የሚኖሩ ሕዝቦች የእምነት ነፃነት እዲከበር ጠየቁ

የቅድስት መንበር ዋና ጸሐፊ ብፁዕ ካርዲናል ፒየትሮ ፓሮሊን፥ በመከራ ውስጥ ለምትገኝ ቤተ ክርስቲያን ዕርዳታን የሚለግስ ጳጳሳዊ ፋውንዴሽን የሃይማኖት ነፃነት በማስመልከት በቫቲካን ያወጣውን የ2025 ዓ. ም. (እአአ) ሪፖርት ተመልክተዋል።

የዚህ ዝግጅት አቅራቢ ዮሐንስ መኰንን - ቫቲካን

ብፁዕ ካርዲናል ፒዬትሮ ፓሮሊን ማክሰኞ ጥቅምት 11/2018 ዓ. ም. በቫቲካን የቀረበውን የ2025 ዓ. ም. (እአአ) የሃይማኖት ነፃነት ሪፖርት መሠረት በማድረግ ባደረጉት የመክፈቻ ንግግር፥ “የሃይማኖት ነፃነት የሰው ልጅ መሠረታዊ ገጽታ ነው” ሲሉ ተናግረዋል።

“እግዚአብሔር ለሰው ልጅ የሰጠው ነፃነት በግል፣ በማኅበረሰብ ወይም በመንግሥት መረገጥ የለበትም” ያሉት ብፁዕ ካርዲናል ፒዬትሮ ፓሮሊን፥ “በየትኛውም አካባቢ የሚገኙ ሕዝቦች በእምነታቸው ላይ ከሚደርስ ማንኛውም ጫና ነፃ መሆን ይገባቸዋል” ብለው ይህም “ከስውር ማኅበራዊ ጫናዎች ሆነ ከመንግሥት አስገዳጅ ትእዛዝ ነፃ” ሊሆኑ ይገባል” ብለዋል።

ብጹዕ ካርዲናል ፓሮሊን አክለውም፥ “ነፃነት የውሸት ማረጋገጫ ወይም በግዴለሽነት ስህተትን ለመቀበል የተፈቀደ ማለፊያ አይደለም” ብለው፥ “ይልቁንም እውነትን በትጋት እንድንከታተል የቀረበ ግብዣ በመሆኑ ሁሉም ሰው ለሞራል ተጠያቂነት የተጠራ ነው” ሲሉ አስረድተዋል።

የሪፖርቱ አሳሳቢ ውጤቶች

የቅድስት መንበር ዋና ጸሐፊ ብፁዕ ካርዲናል ፒየትሮ ፓሮሊን፥ ዘንድሮ 25ኛ ዓመቱን ያከበረውን ሪፖርት በማስመልከት እንደገለጹት፥ “ከዓለም ሕዝብ ውስጥ ወደ ሁለት ሦስተኛ የሚጠጋው ከባድ የሃይማኖት ነፃነት በሚጣስባቸው አገሮች ውስጥ እንደሚኖር” ማለትም ወደ አምስት ቢሊዮን አራት መቶ ሚሊዮን የሚጠጉ ሰዎች እንደሚጎዱ አስረድተዋል።

የ 2025 (እአአ) ሪፖርት ከተመሠረተበት ጊዜ ጀምሮ በትልቅነቱ የላቀ ነው” በማለት የተናገሩት ብጹዕነታቸው፥ በመቀጠልም ይህንን ክስተት በተመለከተ ጠቃሚ የመረጃ እና የትንተና ምንጭ መሆኑን ገልጸዋል።

የሃይማኖት ነፃነት አስፈላጊነት

ብጹዕ ካርዲናል ፓሮሊን የዚህን ዘገባ አስፈላጊነት እና ሰላማዊ ማኅበረሰቦችን ለመገንባት የሃይማኖት ነፃነት እንደሚያስፈልግ በማመላከት፥ በቅርቡ ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ሊዮ አሥራ አራተኛ፥ በመከራ ውስጥ ለምትገኝ ቤተ ክርስቲያን ዕርዳታን የሚለግስ ጳጳሳዊ ፋውንዴሽን ልዑካን ያደረጉትን ንግግር ጠቅሰዋል። ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ሊዮ በንግግራቸው እንዳብራሩት፥ “ይህ ምንጭ ድምፅ ለሌላቸው ድምጽ የሚሰጥ እና የብዙዎችን ስውር ስቃይ የሚገልጥ ኃያል መሣሪያ ነው” ማለታቸውን ብፁዕ ካርዲናል ፓሮሊን ተናግረዋል።

ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ሊዮ በተጨማሪም “የሃይማኖት ነፃነት አማራጭ ሳይሆን አስፈላጊ ነው” በማለት እያንዳንዱ ሰው በአምላክ አምሳል ከተፈጠረው ፍጥረት ጋር የተቆራኘ በመሆኑ፥ “እያንዳንዱ ነፍስ እውነትን እንዲከተል እና ፍትሃዊ ማኅበረሰብን እንዲገነባ ኃይል ይሰጣል” ብለዋል።

“ያለዚህ ነፃነት የኅብረተሰቡ ሥነ-ምግባራዊ መዋቅር መበላሸቱ የማይቀር በመሆኑ ይህም ወደ ግጭት ይመራል” ሲሉ አስጠንቅቀው፥ ካቶሊካዊት ቤተ ክርስቲያን ለሃይማኖት ነፃነት የምትሰጠውን ጥበቃ የሚያጠናክር በመሆኑ በማንኛውም አገር ሕጋዊ እና ተቋማዊ ሕይወት ውስጥ መታወቅ እንዳለበት አሳስበዋል።

ብጹዕ ካርዲናል ፓሮሊን የርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ሊዮን ቃል በመጥቀስ እንደተናገሩት፥ “የሃይማኖት ነፃነት ረቂቅ ሆኖ መቆየት እንደማይችል ነገር ግን በግለሰቦች እና በማኅበረሰቦች የዕለት ተዕለት ሕይወት ውስጥ መተዳደር፣ መጠበቅ እና መስፋፋት አለበት” ብለዋል።

የሰብዓዊ መብቶች መግለጫ አንቀጽ 18

ብፁዕ ካርዲናል ፓሮሊን በንግግራቸው፥ የሃይማኖት ነፃነት ለዓለማችን ያለውን ጠቀሜታ የሚያሳዩ ሁለት አስፈላጊ ሠነዶችን በማስታወስ፥ የመጀመሪያው “Dignitatis Humanae” ወይም “የሰው ልጅ ክብር” በሚል ርዕሥ ሁለተኛው የቫቲካን ጉባኤ ይፋ ያደረገው ሐዋርያዊ ሠነድ ሲሆን፥ የታተመበትን 60ኛ ዓመት ዘንድሮ እንደሚያከብር ታውቋል።

ሁለተኛው፥ የዓለም አቀፉ የሰብዓዊ መብቶች መግለጫ አንቀጽ 18 የወቅቱ የሰብዓዊ መብቶች ግንባታ የማዕዘን ድንጋይ የሆነው እና ከሁለተኛው የዓለም ጦርነት ወደር የለሽ ጭካኔዎች በኋላ የወጣው “አቻ” የተሰኘ ሠነድ ነው።

ይህ መጣጥፍ የሃይማኖት ነፃነትን አስፈላጊነት በትክክለኛነት ያብራራ ሲሆን፥ የግለሰቦች እምነት ቅድስና በዘዴ የተሰረዘባቸውን እና ሌሎች በርካታ ጭካኔያዊ ተግባራት ያስከተሏቸውን ጠቅላላ ርዕዮተ ዓለሞችን ውድቅ ማድረግን ይደግፋል” ሲሉ ብጹዕነታቸው ተናግረዋል።

“የሃይማኖት ነፃነት ጊዜያዊ መብት ሳይሆን የማይገሰስ መብት በመሆኑ የሰውን አቅም ሙሉ በሙሉ እውን ለማድረግ የግድ አስፈላጊ ነው” ሲል አፅንኦት ሰጥተው፥ የጳጳሳዊ ፋውንዴሽን ወቅታዊ ሪፖርት እንደሚያሳየው፥ የሰብዓዊ መብቶች መግለጫ አንቀጽ 18 ዛሬ በአስጨናቂው የመከራ አዙሪት ውስጥ በቀላሉ የማይሰረዝ መሆኑን ገልጸዋል።

የ “የሰው ልጅ ክብር” ሐዋርያዊ ሠነድ ተጽዕኖ

ብጹዕ ካርዲናል ፓሮሊን “የሰው ልጅ ክብር” ሐዋርያዊ ሠነድ፥ ማኅበረሰቦች እውነትን ከማሳደድ ይልቅ ድልድይ እንዲሠሩ የሚያበረታታ፣ ኃላፊነት የሚሰማው የነጻነት መንገድን ይገነባል” ብለዋል። ይህ ራዕይ ከዚያን ጊዜ ጀምሮ የካቶሊክ እምነት ተከታዮች እንደ የተባበሩት መንግሥታት ባሉ ዓለም አቀፍ ድርጅቶች ውስጥ እንዲሳተፉ እና በሃይማኖታዊ ስደት ላይ የሚደረጉ እንቅስቃሴዎችን የሚያበረታታ መሆኑን ገልጸዋል።

“በትክክል ከታዘዙት የነፃነት መብት ብቻ ሳይሆን የእውነት መንገድ እና ከእግዚአብሔር እና ከጎረቤት ጋር ያለን ግንኙነት መሆኑን ለማስታወስ ያገለግላል” ብለው፥ “የሰው ልጅ ክብር” ሐዋርያዊ ሠነድ ማዕከላዊ መልዕክት፥ ግለሰብ እና ማኅበረሰቦች በሃይማኖታዊ ጉዳዮች ላይ የማኅበረሰብ እና የሲቪል ነፃነት መብት ነው" ብለዋል።

“እምነት ለመለኮታዊ ግብዣ የሚሰጥ ነፃ ምላሽ እንጂ ተገዶ የሚደረግ መሆን የለበትም” ሲሉ የተናገሩት ብጹዕ ካርዲናል ፓሮሊን፥ ምክንያቱም “በእግዚአብሔር አምሳል ለተፈጠሩት የሰው ልጆች ሁሉ የተፈጥሮ ክብር” እውቅናን ከመስጠት የመነጨ ነው” ብለዋል። ሪፖርቱ በብርቱነት እንደገለጸው፥ “እውነት በራሱ እውነት ካልሆነ በቀር ሊጫን አይችልም” ሲሉ  ተናግረዋል።

የሲቪል ባለስልጣናት እና ዓለም አቀፍ ስምምነቶች ሚና

“የሃይማኖት ነፃነት መርህ በሁሉም የሰው ልጆች መስተጋብር ውስጥ በግለሰብም ሆነ በቡድን እንደሚሠራ እና በሕገ መንግሥቱ፣ በአገር ውስጥ ሕጎች እና በዓለም አቀፍ ስምምነቶች ውስጥ እንደ መሠረታዊ የዜጎች መብት መረጋገጥ እንዳለበት ጠቁመዋል።

ሆኖም የሃይማኖት ነፃነት ያልተጣራ ፍፁም ተደርጎ ሊወሰድ እንደማይገባ ይልቁንም በጥበብ እና በፍትሃዊነት የታሰረ እንደሆነ አስረድተው፥ የፖለቲካ ጥንቁቅነት በጋራ ጥቅም ጥያቄዎች የተቀረጹ ድንበሮችን ለመፍጠር ጥቅም ላይ መዋል እንዳለበት በማሳሰብ፥ የሲቪል ባለስልጣናት የማይለዋወጥ የሞራል ህግን በማውጣት ረገድ ወሳኝ ሚና እንዳለው አስረድተዋል።

የቅድስት መንበር ዋና ጸሐፊ ብፁዕ ካርዲናል ፒየትሮ ፓሮሊን በመጨረሻም፥ “የሰው ልጅ ክብር” ሐዋርያዊ ሠነድ የዜጎችን መብት መጠበቅ፣ የህዝብን ሰላም መንከባከብ እና ሞራል መጠበቅን ጨምሮ የሃይማኖት ነፃነት ጥሰቶችን በመከላከል በርካታ ምክንያቶችን እንደሚያቀርብ አፅንዖት ሰጥተዋል።

22 Oct 2025, 18:07