
ጳጳሳዊ የሕይወት ከፍተኛ የትምህርት ተቋም 'የዓለም ፍጻሜ?' በሚል ጭብጥ ጠቅላላ ጉባኤውን አካሄደ
አቅራቢ ዘላለም ኃይሉ ፥ አዲስ አበባ
ጳጳሳዊ የሕይወት ከፍተኛ የትምህርት ተቋም “የዓለም መጨረሻ? ግጭቶች፣ ኃላፊነቶች እና ተስፋዎች” በሚል መሪ ሃሳብ በሮም በሚገኘው ኦገስቲያነም ኢንስቲትዩት ከየካቲት 24-26 ቀን 2017 ዓ.ም. ድረስ የጎረጎሳዊያኑን የ 2025 ጠቅላላ ጉባኤውን እያካሄደ እንደሚገኝ የተገለጸ ሲሆን፥ በዚህ ዓለም አቀፍ ጉባኤ ላይ የኖቤል ተሸላሚዎች፣ የሥነ ህዋ ተመራማሪዎች፣ የፊዚክስ ሊቃውንት፣ ባዮሎጂስቶች፣ የቅሪተ አካል ተመራማሪዎች፣ የሃይማኖት ሊቃውንት እና የታሪክ ምሁራን በጉባኤው ላይ እንደሚገኙ የቅድስት መንበር ጋዜጣዊ መግለጫ ጽህፈት ቤት ሰኞ ዕለት ባወጣው መግለጫ ይፋ አድርጓል።
ጋዜጣዊ መግለጫውን ከሰጡት ውስጥ የጳጳሳዊ የሕይወት አካዳሚ ፕሬዚዳንት ሊቀ ጳጳስ ቪንቸንዞ ፓግሊያ፣ ፕሮፌሰር ካታሊን ካሪኮ የ2023 በሕክምና የኖቤል ተሸላሚ፣ ፕሮፌሰር ጊዶ ቶኔሊ ጣሊያን ከሚገኘው ፒሳ ዩኒቨርሲቲ፣ ፕሮፌሰር ሄንክ ቴን ሜክሲኮ ሲቲ ከሚገኘው አናሁዋክ ዩኒቨርሲቲ እና እህት ጊስቲና ሆልሃ ከዩክሬን ይገኙበታል።
ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንቺስኮስ ለጉባኤው ተሳታፊዎች የማበረታቻ መልዕክት የላኩ ሲሆን፥ ይህንንም መልዕክት የጋዜጣዊ መግለጫ ጽህፈት ቤቱ ሰኞ ዕለት አሳትሞ ለንባብ ማቅረቡ ተገልጿል።
ከጋዜጣዊ መግለጫው በፊት የቅድስት መንበር ጋዜጣዊ መግለጫ ጽህፈት ቤት ምክትል ዋና ዳይሬክተር ክሪስቲያን መሬይ እንዳረጋገጡት ሮም በሚገኘው ጀሚሊ ሆስፒታል የድርብ ሳምባ ምች ሕክምና እየተከታተሉ ለሚገኙት ለርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንቺስኮስ ሁሉም ሰው በጋራ በመሆን ጸሎት እንዳደረጉላቸው ገልጸዋል።
ሊቀ ጳጳስ ቪንቼንዞ ፓግሊያ የዝግጅቱ መሪ ቃል ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንቺስኮስ ቀደም ብለው የተገነዘቡትን “ፖለቲካዊ ቀውስ” ላይ ግንዛቤን እንደሚፈጥር ያመላከቱ ሲሆን፥ ሊቀ ጳጳሱ እንዳሉት ፕላኔቷን ለአደጋ እያጋለጡ ከሚገኙት እና እንዲያውም እኛን “በአደጋው ውስጥ ‘ለማስመጥ’ በሚጥሩት አስደናቂ እውነታዎች መካከል ብንሆንም ሁሉም ሰው በአንድነት ከተሰባሰበ ይህን ክስተት መቋቋም እና መከላከል እንችላለን ብለዋል።
የኖቤል ተሸላሚ የሆኑት ዶክተር ካሪኮ በበኩላቸው በተለይ በዓለም ዙሪያ እየተከሰቱ ባሉ አስከፊ ነገሮች መካከል ሳይንቲስቶች እና ባለሙያዎች አብረው ጉልህ ስኬት እንዲያስመዘግቡ የሚያስችላቸው ብዙ የጋራ ጉዳዮች መኖራቸውን በማስታወስ፥ በጉባኤው ላይ በመገኘታቸው የተሰማቸውን ደስታ ገልጸው፥ በተለይም ውይይቶችን ለመከታተልና የመፍትሄ ሃሳቦችን በጋራ ለመውሰድ ያላቸውን ትልቅ ተስፋ ገልጸዋል።
ከፒሳ ዩኒቨርሲቲ የመጡት ፕሮፌሰር ጊዶ ቶኔሊ በሳይንስ እና በቴክኖሎጂ ሂደት ውስጥ በዝግመተ ለውጥ እና በእነዚህም ለውጦች ምክንያት ህይወታችን እንዴት “በአስደናቂ ሁኔታ እንደተቀየረ” የገለጹ ሲሆን፥ በተመሳሳይ ሁኔታ ተከታታይ አደጋዎችን ጨምሮ፥ የቴክኖሎጂ እድገቶች ለሰው ልጅ ብዙ እድሎችን እና እድገቶችን እንደሚያቀርቡ ተናግረዋል።
ሜክሲኮ ሲቲ ከሚገኘው አናሁዋክ ዩኒቨርሲቲ የመጡት ፕሮፌሰር ሄንክ ቴን በበኩላቸው በተለያዩ ጥናቶች መሰረት ምን ያህል ወጣቶች ስለ ወደፊቱ ጊዜ በጣም ተስፋ እንደሚቆርጡ በትምህርታዊ ጥናት በማስደገፍ እይታቸውን አቅርበዋል። ከዚህ በመነሳት ለዚህ ጥፋትና ጨለማ አመለካከት መፍትሄ ለመስጠት ትምህርት ቁልፍ ሚና እንዳለው ጠቁመው፥ ይህም አዲስ ክስተት ሳይሆን ከዚህ በፊት ተሞክሮ ውጤታማ የሆነ ነው ብለዋል። ስለሆነም እነዚህን አመለካከቶች ታሪካዊ በሆነ ሁኔታ ውስጥ ማስቀመጥ አስፈላጊ መሆኑን ጭምር አብራርቷል።
ከዩክሬን የመጡት ተሸላሚዋ እህት ጊስቲና ሆልሃ በዩክሬን ብሔራዊ የሕክምና ሳይንስ አካዳሚ የዘር ውርስ የበሽታ ጥናት ተቋም ውስጥ በሚገኘው በሊቪቭ ሜዲካል ጄኔቲክ ማዕከል ውስጥ ክሊኒካል ሳይኮሎጂስት በመሆን ባካበቱት ልምድ በመነሳት ንግግር አድርገዋል።
ብዙውን ጊዜ ዶክተሮች በአብዛኛው ፅንስ ማስወረድን የሚያስከትሉ የተወሰኑ የወሊድ እና በዘር የሚተላለፉ ችግሮችን የሚያሳዩ የቅድመ ወሊድ ምርመራዎች እንደሚያደርጉ በመጥቀስ፥ ነገር ግን ፅንሱን ላለማቋረጥ እና እርግዝናውን ለመቀጠል የሚወሰኑ ጥንዶች መኖራቸውን አስታውሰዋል።
ሲስተር ጊስቲና የሚያገለግሉበት ‘ፔሪናታል ሆስፒክ’ የጨቅላ ህፃናት እንክብካቤ ማዕከል እንቅስቃሴውን የጀመረው እ.አ.አ. በ 2013 ዓ.ም. ሲሆን፥ ተቋሙ እስከ 2017 ዓ.ም. በሌቪቭ ውስጥ ከሰራ በኋላ ወላጆችን እና በጠና የታመሙ ልጆቻቸውን በከፍተኛ ደረጃ ብቁ እና ሁለገብ እንክብካቤን የመስጠት አገልግሎቱን ወደ ሌሎች የዩክሬን ከተሞች አስፋፍቷል።
ሲስተር ጊስቲና እንደገለጹት ከብዙ ሀገራት ልምድ በመነሳት ባለፉት አስርት ዓመታት ውስጥ ተቋሙ ለልጆች እውነተኛ የፍቅር ቦታ እንደሚሰጥ እና በባለሙያዎች ቡድን ልጁ እስኪወለድ ድረስ ለወላጆች እና ለዘመዶቻቸው ድጋፍ እንደሚሰጥ በበርካቶች ዘንድ የግንዛቤ እድገት እንዳመጣ ማየታቸውን ተናግረዋል።
በዚህ ስራ እና ቁርጠኝነት አማካይነት ለዚህ ችግር ለተጋለጡ ጥንዶች በህክምና፣ በስነ ልቦና፣ በማህበራዊ እና በመንፈሳዊ ደረጃ ተገቢው እገዛ እንደሚደረግላቸው ገልጸዋል።