ር.ሊ.ጳ ሊዮ በሰው ሰራሽ አስተውሎት ዘመን ቤተሰብ የመጀመሪያው የሰብአዊነት ትምህርት ቤት ነው አሉ።
የእዚህ ዝግጅት አቅራቢ መብራቱ ኃ/ጊዮርጊስ-ቫቲካን
"ጤናማ ሕግ መሰረታዊ የሰብአዊ መብቶችን እና ነጻነቶችን በመጠበቅ ሳይንሳዊ እና ቴክኖሎጂያዊ ፈጠራን ማበረታታት አለበት። ተጠቃሚዎችን ከብዝበዛ መጠበቅ፣ የግል ምስጢሮችን መጠበቅ፣ አዳዲስ ቴክኖሎጂዎችን አጠቃቀም ግልጽነት ማረጋገጥ እና ዴሞክራሲያዊ ተቋማትን ማጠናከር እንዳለባቸው ማረጋገጥ አለበት" ብለዋል።
ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ሊዮ 14ኛ ዓርብ ዕለት በቫቲካን ለዓለም አቀፍ የካቶሊክ ሕግ አውጪዎች መረብ ይህንን እምነታቸውን የገለጹ ሲሆን ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳቱ በሕግ አውጭው ስብሰባ፣ "ጠንካራ የሕግ ማዕቀፎች፣ ገለልተኛ ቁጥጥር፣ መረጃ ያላቸው ተጠቃሚዎች እና ኃላፊነቱን የማይሽር የፖለቲካ ሥርዓት አስፈላጊ ናቸው" ብለዋል።
እንዲህ ዓይነቱ ቁጥጥር በተለያዩ ደረጃዎች - አካባቢያዊ፣ ብሄራዊ እና ዓለም አቀፍ - "የተሳተፉትን የሥነ ምግባር ማዕቀፎች ግልጽ ውይይት በማድረግ እና ለጋራ የማህበራዊ ፍትህ ደረጃዎች ተገዢ ለማድረግ" እንደሚረዳ የገለጹ ቅዱስነታቸው፣ "በአርቴፊሻል ኢንተለጀንስ ስርዓቶች ውስጥ የተካተቱትን እሴቶች የሚገድብ አንድም ርዕዮተ ዓለም ወይም ፍላጎት እንዳይኖር" ያረጋግጣሉ ሲሉ ተናግረዋል።
በተመሳሳይ ጊዜ፣ ቅዱስ አባታችን አፅንዖት ሰጥተው እንደ ተናገሩት ከሆነ፣ የአርቴፊሻል ኢንተለጀንስ ፈጣን እድገት አዳዲስ የቴክኖሎጂ ጥገኝነት ዓይነቶችን የመፍጠር አደጋ አለው፣ ድሃ አገሮች በበለጸጉ አገሮች ላይ ጥገኛ እንዲሆኑ ያደርጋል ብለዋል።
ረቂቅ የገዢነት ዓይነቶች
"በዚህ ረገድ ንቁ መሆን አለብን" ብለዋል፣ "ፈጠራ ለርዕዮተ አለማዊ ወይም ኢኮኖሚያዊ ቅኝ ግዛት ሌላ ተመንገድ እንዳይሆን" መጠንቀቅ ይገባናል ያሉት ቅዱስነታቸው በሚያሳዝን ሁኔታ፣ "አልጎሪዝም (ስለተ ቀመር) ማን እንደሚታይ እና ማን እንደማይታይ ሲወስን፣ ዲጂታል መድረኮች ያለ ተጠያቂነት የህዝብ ውይይትን ሲቀርጹ እና የሰራተኞች ክብር ለስርዓቶች ማመቻቸት ሲገዛ ስውር የገዢነት አይነት ይቀርብልናል" ብለዋል።
ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ሊዮ እንዳስጠነቀቁት ከሆነ እንደነዚህ ያሉ እድገቶች፣ ፣ "የበላይነትን የጥንታዊ ፈተና አዲስ ገጽታ ይገልጣሉ" ብለዋል።
ቤተሰብ እንደ የመጀመሪያው የሰው ልጅ ትምህርት ቤት
ቅዱስ አባታችን ከዚህ የስልጣን ባህል በመቃወም፣ ቤተክርስቲያን "የፍቅርን ስልጣኔ" ታቀርባለች ያሉ ሲሆን
"በእንደዚህ አይነት ማህበረሰብ ውስጥ" ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ሊዮ እንዳሉት ከሆነ "የሰው ልጅ የመጀመሪያ ትምህርት ቤት ቤተሰብ ይሆናል" ብለዋል።
"በቤተሰብ ውስጥ መጀመሪያ ከስሌት በፊት መተማመንን እንማራለን፣ ከፉክክር በፊት ልግስናን፣ ከመከፋፈል በፊት ውይይትን እና ከስልጣን በፊት ፍቅርን እንማራለን" ብለዋል።
ይህንን በአእምሯቸው ይዘው፣ አርቴፊሻል ኢንተለጀንስ "ይህንን የኅብረተሰብ ዋና ክፍል - ሰዎችንና ግንኙነቶችን ከመረጃና ማስመሰያዎች በመቀነስ፣ ወጣቶችን አእምሮ ፍላጎትን በሚያዛቡ ይዘቶች በማጥለቅለቅ ወይም የቤተሰብን ሕይወት በኢኮኖሚያዊ ሁኔታ አደጋ ላይ በሚጥሉ ኢኮኖሚያዊ ሞዴሎች በማጥለቅለቅ ይህንን የኅብረተሰብ ዋና ክፍል እንዲያፈርስ መፍቀድ የለበትም" ብለዋል።
ጋብቻንና ቤተሰቦችን ማጠናከር
"በዚህ ምክንያት" ቅዱስ አባታችን "ጋብቻንና ቤተሰቦችን የሚያጠናክሩ፣ ወላጆችን በትምህርት ተልእኳቸው እንዲደግፉ እና ወጣቶች የወደፊቱን ጊዜ በልበ ሙሉነት እንዲመለከቱ የሚያስችሉ ፖሊሲዎችን እንድታስተዋውቁ አበረታታችኋለሁ" ያሉ ሲሆን "ውድ ጓደኞቼ፣ ዓለም የሰውን ልጅ ሚና የሚቀንስ አርቴፊሻል ኢንተለጀንስ አያስፈልጋትም፤ ይልቁንም በጥበብ የበራ የሰው ልጅ አስተውሎት፣ በህሊና የሚመራ የፖለቲካ ሥልጣን እና በበጎ አድራጎት የሚመራ የቴክኖሎጂ ፈጠራ ያስፈልገዋል" ሲሉ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ሊዮ አጥብቀው ተናግረዋል።
ይህንን ጊዜ ብቻ ነው ሰው ሰራሽ አስተውሎት (አርቴፊሻል ኢንተለጀንስ) የሰው ልጅ ተቀናቃኝ ሳይሆን የጋራ ጥቅም አገልጋይ የሚሆነው ያሉት ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ሊዮ 14ኛ በእነዚህ ሀሳቦች በበይኔ መረብ የተደረገው ውይይት ለአገሮቻችሁና ለመላው የሰው ልጅ ቤተሰብ ብዙ ፍሬ እንዲያፈሩ እጸልያለሁ በማለት ንግግራቸውን ደምድመዋል።
