ሰኔ 19/1974 ዓ. ም. ሮበርት ፕሬቮስት የክኅነት ማዕረግ የተቀበሉበት ዕለት መሆኑ ተገለጸ
የዚህ ዝግጅት አቅራቢ ዮሐንስ መኰንን - ቫቲካን
ከቫቲካን በጥቂት ርቀት በምትገኝ የቅድስት ሞኒካ ጸሎት ቤት ውስጥ ከ44 ዓመታት በፊት ወጣት ሮበርት ፕሬቮስት በሃያ ሰባት ዓመቱ የክኅነት ማዕረግ መቀበሉ ይታወሳል። ከአምስት ዓመታት ቀደም ብሎ በቅዱስ አጎስጢኖስ ገዳም የማኅበሩን ቃለ መሐላ አድርጎ እንደ ነበር ይታወሳል። በዚያው ዓመት መስከረም ወር ላይ በቅዱስ ቶማስ አኩዊናስ (አንጀሊኩም) ጳጳሳዊ ዩኒቨርሲቲ ሕግ ቀኖናን ለመማር ወደ ሮም መጣ።
ከጥቂት ወራት በኋላ በሚያውቀው ቦታ የክኅነት ማዕረግ ተቀበለ። ፕሬቮስት እንደ ጎርጎሮሳውያኑ ከ2023 ዓ. ም. ጀምሮ በቫቲካን ሕንጻ ውስጥ ይኖሩ ነበር፣ በዚያው ዓመት መስከረም 30 ላይ ነፍስሔር ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንችስኮስ በካርዲናልነት ሾሟቸው።
“እኔ አገልጋያችሁ ነኝ”
ለመታሰቢያነቱ የተዘጋጀች ካርድ በ15ኛው ክፍለ ዘመን በሩሲያዊ ሠዓሊ የተሳለች መንፈሳዊ ምስል የጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የመጨረሻ እራት የምታስታውስ ነበረች። በግብዣ ካርዱ ላይ እንዲታተሙ የተመረጡት ቃላት፥ ቅዱስ አጎስጢኖስን በስብከቱ ቁ. 399 ላይ “ሁላችሁንም መመገብ አልችልም፤ ነገር ግን ይህ ቃል የእናንተ ድርሻ ነው፤ ከተመሳሳይ ማዕድ እመግባችኋለሁ፤ እኔም አገልጋያችሁ ነኝ” ማለቱን ያስታውሳሉ።
ከሀገረ ስብከቱ የተላከ የመልካም ምኞት መግለጫ
በጳጳስነት ካገለገለበት ከሮም ሀገረ ስብከት የተላከው የመልካም ምኞት መግለጫ መልዕክት እንዲህ ይላል፥ “ከፍተኛ ጥንቃቄን የሚፈልግ አገልግሎትዎን በማወቅ፥ መንግሥቱን ለመመስከር እና በየቀኑ ለሰላም በሚያደርጉት ቁርጠኝነት በመታደስ እኛም እንደግፍዎታለን፤ በአዲስ ፍቅር እና በእግዚአብሔር ቅዱስ ሕዝብ ጸሎት የትሑታንን ሰላማዊ ኃይል እየጠራን እንደግፍዎታለን፤ የመለኮታዊ ፍቅር እናት እጅግ ቅድስት ድንግል ማርያም ትጠብቅዎት፤ አገልግሎትዎንም ትባርክልዎት”
