ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ሊዮ 14ኛ በሞንትሴራት የቅዱስ ብሩክ ማኅበር መነኮሳትን አመሰገኑ
የዚህ ዝግጅት አቅራቢ ዮሐንስ መኰንን - ቫቲካን
ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ሊዮ 14ኛ በሞንትሴራት የእመቤታችን ማርያም ገዳም ውስጥ የመቁጠሪያ ጸሎት ካደረሱ በኋላ ንግግር በማድረግ በገዳሙ የተዘጋጀውን የምሳ ግብዣ ከመነኮሳቱ ጋር ተካፍለው ስጦታንም ተለዋውጠዋል።
ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ሊዮ 14ኛ በፔሩ ትሩይሎ የሞንትሴራት እመቤታችን ማርያም ቁምስና መሪ በነበሩበት ወቅት ከሌሎች የቅዱስ አጎስጢኖስ ማኅበርተኞች ጋር ወደ ገዳሙ የሄዱበትን ጊዜ ማስታወሳቸውን የቅድስት መንበር መግለጫ አስታውቋል።
“ቅዱስነታቸው ለዛሬው ስብሰባ እና የገዳሙ መነኮሳት ለእመቤታች ቅድስት ድንግል ማርያም ባላቸው ታማኝነት ለሚሰጡት ምስክርነት አመስግነዋል” ሲል መግለጫው አክሏል።
በዚህ ረገድ ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ሊዮ 14ኛ በዚህ ታሪካዊ ወቅት መነኮሳቱ በተለይ ለቤተ ክርስቲያን እና ለዓለም ለሚሰጡት ውድ ምስክርነት አፅንዖት በመስጠት፥ በጫጫታ፣ በእንቅስቃሴ እና በጥፋት በተሞላ ዓለም ውስጥ ላላቸው የዝምታ ስጦታ አመስግነዋቸዋል።
ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ሊዮ፥ “ዓለም የዝምታ ጊዜን እንድንለማመድ እና እንድንጸልይ የሚጋብዙ ሞዴሎች ያስፈልጉታል” ሲሉ ንግግራቸውን ደምድመዋል።
በገዳሙ ውስጥ ወደ 50 የሚጠጉ የቅዱስ ብሩክ ገዳም መነኮሳት የሚኖሩ ሲሆን ገዳሙ የምሥረታውን ሺህኛ ዓመቱን እንደ ጎርጎሮሳውያኑ በ2025 ዓ. ም. ማክበሩ ይታወሳል።
ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ሊዮ 14ኛ በሞንትሴራት የእመቤታችን ገዳም የጎብኚዎች መዝገብ ላይ ባኖሩት የማስታወሻ ቃል፥ “በእናትነት ምልጃዋ መላውን ቤተ ክርስቲያን እንድትጠብቅ በመለመን ሐዋርያዊ አገልግሎቴን በሞንትሴራት እመቤታችን እግር ሥር አስቀምጣለሁ” ሲሉ ጽፈዋል።
ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ሊዮ 14ኛ በእንግድነት ለተቀበሏቸውን የሞንትሴራት እመቤታችን ገዳም መነኮሳትን አመስግነው ቡራኬያቸውን ሰጥተዋቸዋል።
ከግንቦት 29 እስከ ሰኔ 5/2018 ዓ. ም. ድረስ በስፔይን በሚያደርጉት ሐዋርያዊ ጉብኝታቸው ቀደም ሲል ማድሪድን ጎብኝተው ወደ ባርሴሎና ከተጓዙ በኋላ የካናሪ ደሴቶችንም እንደሚጎበኟቸው ታውቋል።
