ፈልግ

ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ሊዮ 14ኛ ለአንድ ወጣት የድቁና ማዕረግ ሲሰጡ ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ሊዮ 14ኛ ለአንድ ወጣት የድቁና ማዕረግ ሲሰጡ   (ANSA)

ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ሊዮ 14ኛ፥ “መንፈሳዊ ጥሪ የእግዚአብሔር ስጦታ ውስጣዊ ግኝት ነው” ሲሉ ገለጹ

ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ሊዮ 14ኛ ዘንድሮ በሚያዝያ ወር የሚከበረው የዓለም የጥሪ ጸሎት ቀን መልዕክት ይፋ አድርገዋል። ቅዱስነታቸው በመልዕክታቸው “እያንዳንዱ ጥሪ ለቤተ ክርስቲያን እና ጥሪውን በደስታ ለሚቀበሉት በሙሉ እጅግ ጥሩ ስጦታ እንደሆነ አስገንዝበዋል።

የዚህ ዝግጅት አቅራቢ ዮሐንስ መኰንን - ቫቲካን

ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ሊዮ 14ኛ እሑድ ሚያዝያ 18/2018 ዓ. ም. የሚከበረውን 63ኛ የዓለም የጥሪ ጸሎት ቀን መልዕክት አስተላልፈዋል።

ቅዱስነታቸው ዕለቱን “በጥሪ ውስጣዊ ገጽታ ላይ አንዳንድ አስተያየቶችን የምንለዋወጥበት የጸጋ አጋጣሚ፣ በልባችን ውስጥ የሚያብበው የእግዚአብሔር ነፃ ስጦታ ግኝት” ሲሉ ጠርተውታል። እንዲሁም “መልካሙ እረኛ የሚመራንን በእውነት ውብ የሆነውን የሕይወት መንገድ አብረን ለመፈለግ ዕድል የምናገኝበት ነው” ብለውታል።

የኢየሱስ ክርስቶስ ውበት እኛንም ውብ ያደርገናል

በዮሐንስ ወንጌል ውስጥ ኢየሱስ ክርስቶስ ራሱን “መልካም እረኛ” ሲል መግለጹን ያስታወሱት ቅዱስነታቸው፥ “ሕይወቱን ለበጎቹ ለመስጠት ዝግጁ እንደሆነ፣ በዚህም የእግዚአብሔርን ፍቅር እንደሚገልጽ እና እርሱን ሲከተሉት ሕይወት በእርግጥም ውብ እንደሚሆን የሚገልጽ እረኛ ነው” በማለት አፅንዖት ሰጥተዋል።

ይህንን ውበት ለይቶ ለማወቅ ማሰላሰል እና ውስጣዊነት እንደሚያስፈልግ ገልጸው፥ ተረጋግቶ የሚያዳምጥ፣ የሚጸልይ፣ የእረኛውን እይታ የሚቀበል፣ በእርሱ የሚያምን እና ከእርሱ ጋር ሕይወት በእውነት ውብ ሊሆን ይችላል” የሚል ብቻ በልበ ሙሉነት መናገር እንደሚችል አስረድተዋል።

ቅዱስነታቸው በማከልም አስገራሚው ነገር ደቀ መዝሙሩ በመሆን አንድ ሰው በእውነት ውብ እንደሚሆን እና የእርሱ ውበት በእውነት እንደሚለውጠን ተናግረዋል።

ቅዱስ አጎስጢኖስ ይህ የሕይወት እና የእምነት ተሞክሮ እንደ ነበረው አስታውሰው፥ በወጣትነት ዕድሜው የሠራውን ኃጢአት እና ስህተት በመገንዘብ በጨለማ ውስጥ መሪ የሚሆንለት የመለኮታዊ ብርሃን ውበት ማግኘቱን አስረድተዋል።

የፍቅር እና የደስታ ተሞክሮ

ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ሊዮ 14ኛ ጥሪ አንድ ሰው ብቻው የሚስማማበት አንድ ሞዴል ሳይሆን የፍቅር እና የደስታ ልምድ እንደሆነ ተናግረዋል።

“ስለዚህ ለውስጣዊ ሕይወት በምንሰጠው እንክብካቤ ላይ በመመስረት የጥሪ አገልግሎታችንን በአስቸኳይ መጀመር እና ለወንጌል ምስክርነት ያለንን ቁርጠኝነት ማደስ አለብን” ብለዋል።

ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ሊዮ 14ኛ በዚህ ምክንያት “ቤተሰቦች፣ ቁምስናዎች፣ ገዳማውያን እና ገዳማውያት፣ ጳጳሳት፣ ካህናት፣ ዲያቆናት፣ የትምህርተ ክርስቶስ መምህራን፣ አስተማሪዎች እና ምእመናን በሙሉ ይህንን ስጦታ ተቀብለው እንዲንከባከቡት፣ እንዲጠበቁት እና ወደፊት እንዲያራምዱት የሚያስችሏቸውን ሁኔታዎች ለመፍጠር ራሳቸውን ሙሉ በሙሉ እንዲወስኑ ጥሪ አቅርበዋል።

“የእግዚአብሔር ጥሪ መብቀል እና ማደግ የሚችለው አካባቢያችን በሕያው እምነት ሲበራ፣ በማያቋርጥ ጸሎት ሲደገፍ እና በወንድማማችነት አብሮ ሲበለጽግ ብቻ ነው” ብለዋል።

የእግዚአብሔር ፍቅራዊ እይታ ልባችንን ያበራል

“እግዚአብሔር እኛን ያውቀናል፣ ልባችንንም በፍቅር እይታው ያበራልናል” ያሉት ቅዱስነታቸው፥ እያንዳንዱ ጥሪ የሚጀምረው ፍቅር በሆነው በእግዚአብሔር ግንዛቤ እና ተሞክሮ እንደሆነ አስረድተው፥ በጥልቀት የሚያውቀን እግዚአብሔር ለእያንዳንዱ ሰው ልዩ የቅድስና እና የአገልግሎት መንገድን አስቀድሞ አስቀምጧል” ብለዋል።

ነገር ግን ይህ ግንዛቤ እግዚአብሔርን በጸሎት እንድናውቀው፣ ቃሉን እንድንሰማ፣ ቅዱሳት ምስጢራትን እንድንቀበል እና በቤተ ክርስቲያን ሕይወት ውስጥ ለወንድሞቻችን እና ለእህቶቻችን በሚደረጉ የበጎ አድራጎት ሥራዎች በኩል እንድንረዳ ተጋብዘናል” ሲሉ አፅንዖት ሰጥተዋል።

“እያንዳንዱ ጥሪ ለቤተ ክርስቲያን ወደር የሌለው ስጦታ ነው!”

ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ሊዮ 14ኛ ወጣቶችን ወደ ሙሉ እና ፍሬያማ ሕይወት የሚጋብዛቸውን የእግዚአብሔርን ድምፅ እንዲያዳምጡ ጥሪ በማቅረብ፥ ተሰጥኦአቸውን እንዲጠቀሙበት፣ አቅማቸውን እና ድክመቶቻቸውን ከተከበረው የኢየሱስ ክርስቶስ መስቀል ጋር እንዲያጣምሩ ጥሪ አቅርበዋል።

ወጣቶች እግዚአብሔርን ለማወቅ ጊዜያቸውን ለቅዱስ ቁርባን አምልኮ እንዲመድቡ፣ የእግዚአብሔርን ቃል በታማኝነት እንዲያሰላስሉ፣ በየቀኑ ተግባራዊ እንዲያደርጉት እና በቤተ ክርስቲያን የቅዱስ ቁርባን ሕይወት ላይ በንቃት እና በሙላት እንዲሳተፉ አሳስበዋል።

“ወጣቶች ከኢየሱስ ክርስቶስ ጋር ባላቸው የጠበቀ ወዳጅነት አማካኝነት፣ በጋብቻ ሕይወት፣ በክህነት አገልግሎት፣ በቋሚ የዲቁና ወይም በምንኩስና ሕይወት ራሳቸውን እንዴት መስጠት እንደሚችሉ ይማራሉ” ብለው፥ “እያንዳንዱ ጥሪ ለቤተ ክርስቲያን እና በደስታ ለሚቀበሉት ወደር የሌለው ስጦታ ነው” ሲሉ አስረድተዋል።

ቅዱስ ዮሴፍ ሁሉም ነገር እርግጠኛ ባልሆነበት ጊዜም ያምን ነበር

ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ሊዮ 14ኛ፥ እግዚአብሔርን ማወቅ ማለት ከሁሉም በላይ እራስን ለእርሱ አደራ መስጠትን መማር ማለት እንደሆነ አስታውሰው፥ የእርሱ እቅዶች የእኛን እቅድ ሲያበላሹ እንኳ ሕይወት እራሱን በጌታ ላይ የመታመን እና ራሳችንን ለእርሱ የመተው ዘላቂ ተግባር መሆኑን አስረድትዋል።

በተለይም ምስጢራዊ እና ባልተጠበቀ ጊዜ በተከሰተ የቅድስት ድንግል ማርያም እርግዝና ወቅት በሕልም የተገለጠውን መለኮታዊ መልዕክት ያመነውን እና እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምን እና ልጇን በታዛዥ ልብ የተቀበለውን ቅዱስ ዮሴፍን ጠቅሰዋል።

“የናዝሬቱ ዮሴፍ በእግዚአብሔር እቅዶች ላይ ሙሉ በሙሉ የመታመን ምሳሌ ነው” ያሉት ቅዱስነታቸው፥ ቅዱስ ዮሴፍ በዙሪያው ያለው ነገር በሙሉ ጨለማ እና እርግጠኛ ባልሆነበት ሁኔታ ውስጥ እና ክስተቶችም ከራሱ እቅዶች የተለዩ ሲመስሉም ያምን እንደ ነበረ እና ራሱንም ለእግዚአብሔር አደራ ሰጥቶ ነበር” ብለዋል።

ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ሊዮ 14ኛ እግዚአብሔር በጨለማ ሰዓታችን ውስጥ የማይተወን መሆኑን አስታውሰው፥ በብርሃኑም እያንዳንዱን ጥላ ለማስወገድ እንደሚመጣ አስረድተው፥ በፈተናዎች እና በችግሮች መካከል እንኳን በመንፈሱ ብርሃን እና በጥንካሬው ጥሪያችን እያደገ እና እየበሰለ እንደሚሄድ፣ ቁስል እና ውድቀት ቢኖረንም በታማኝነት እና በእምነት የተቀረጸ ውበት የበለጠ ሙሉ በሙሉ ሲያንጸባርቅ ማየት እንችላለን” ብለዋል።

በእያንዳንዱ የሕይወት ሁኔታ ከኢየሱስ ጋር መሆን አለብን

ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ሊዮ 14ኛ “ጥሪ በአንድ ቦታ ላይ የተወሰነ ሳይሆን ነገር ግን ከእግዚአብሔር ጋር ባለን ቅርበት የሚቀጥል እና የሚያድግ ሂደት ነው” ብለው፥ መንፈስ ቅዱስ በልባችን እና በሕይወት ውስጥ እንዲሠራ በመፍቀድ እና ሁሉንም ነገር በዚህ የብርሃን ስጦታ እንደገና በመተርጎም ከኢየሱስ ጋር መሆን አለብን” ሲሉ ተናግረዋል።

“እንደ ወይኑ እና የወይኑ ቅርንጫፎች መላ ሕይወታችን ከእግዚአብሔር ጋር ባለን ጠንካራ እና ወሳኝ ትስስር በፈተና ጊዜ ልባችን ምላሽ መስጠት አለበት” ብለዋል።

ጥሪ ከእግዚአብሔር ጋር በሚደርግ ዕለታዊ ግንኙነት ማደግ አለበት

ስለዚህ ጥሪ ወዲያውኑ ለሌላ የሚተላለፍ ንብረት ወይም ለአንዴ እና ለመጨረሻ ጊዜ የሚሰጥ ሳይሆን ነገር ግን ልክ እንደ ሕይወት በራሱ ጊዜ የሚገለጥ መንገድ ነው” ብለው፥ የተቀበልነው ስጦታ እንዲያድግ እና ፍሬን እንዲያፈራ ከእግዚአብሔር ጋር ዕለት በዕለት በመገናኘት ማደግ አለበት” ብለዋል።

ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ሊዮ 14ኛ እያንዳንዱ ሰው በየቀኑ በጸሎት እና በቃሉ ላይ በማሰላሰል ከእግዚአብሔር ጋር ያለውን የግል ግንኙነት እንዲያዳብር ጥሪ አቅርበዋል።

“ቆም ብሎ በማዳመጥ ራስን ለእግዚአብሔር በአደራ መስጠት ያስፈልጋል” ብለው፥ በዚህ መንገድ የጥሪ ስጦታ አድጎ ለቤተ ክርስቲያን እና ለዓለም ደስታን በማምጣት የተትረፈረፈ ፍሬ ያፈራል” ሲሉ አስገንዝበዋል።

ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ሊዮ በመጨረሻም፥ መለኮታዊ ስጦታዎችን የመቀበል እና በጸሎት የማዳመጥ ስጦታ ምሳሌ የሆነች እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም በዚህ ጉዞ ወቅት ዘወትር ከእናንተ ጋር እንድትሆን!” በማለት ተጽኖአቸውን አቅርበዋል።

26 Mar 2026, 15:54