ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ሊዮ፡ በኢራን የጦር መሳሪያዎች ጸጥ እንዲሉ ጥሪ አቀረቡ!
የዚህ ዝግጅት አቅራቢ መብራቱ ኃ/ጊዮርጊስ-ቫቲካን
በእሁድ ዕለት በቅዱስ ጴጥሮስ አደባባይ የመልአከ እግዚአብሔር ጸሎት ካደረጉ በኋላ፣ የርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ሊዮ ሀሳባችውን ወደ መካከለኛው ምስራቅ አዙረው “ከፍተኛ ድንጋጤ የሚፈጥር ዜና እየመጣ ነው” ብለዋል።
በቅዱስ ጴጥሮስ አደባባይ ለተሰበሰቡት ወደ አስራ አምስት ሺህ የሚጠጉ ምዕመናን ንግግር ሲያደርጉ፣ በተለይም በኢራን እና በክልሉ ውስጥ “ዓመፅ እና ውድመት” እና “ሰፊ የጥላቻ እና የፍርሃት ድባብ” እንዳለ ጠቅሰዋል።
በተጨማሪም ግጭቱ እንደ “የተወደደችው ሊባኖስ” ያሉ በአቅራቢያ ያሉ አገሮችን እንደገና “ወደ አለመረጋጋት” ሊያመራ ይችላል የሚለውን ስጋት አፅንዖት ሰጥተው ተናግረዋል።
ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ሊዮ አድማጮቻቸውን “የቦምብ ጩኸት እንዲቆም፣ የጦር መሳሪያዎች ጸጥ እንዲሉ፣ የውይይት ቦታ እንዲከፈት፣ የሕዝቡም ድምፅ እንዲሰማ” እንዲጸልዩ ጋብዘዋል።
ጸሎታቸውን የሰላም ንግሥት ለሆነችው ለማርያም አደራ እንደሚሰጡ ተናግረዋል። እሷም “በጦርነት ምክንያት ለሚሰቃዩት አማላጅ” እና “ልቦችን በማስታረቅና በተስፋ ጎዳናዎች እንድትመራ” ጠይቀዋል።
ሰላም የሚገነባው በዛቻ አይደለም።
ከሳምንት በፊት፣ ባለፈው እሁድ በተካሄደው የመላከ እግዚአብሔር ጸሎት ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ሊዮ 14ኛ በመካከለኛው ምስራቅ እና በኢራን ስላለው ሁኔታ ያላቸውን “ጥልቅ ስጋት” ገልጸው ነበር።
“መረጋጋትና ሰላም የሚገነቡት በጋራ ዛቻዎች ወይም ጥፋትን፣ ህመምንና ሞትን በሚዘሩ መሳሪያዎች ሳይሆን በተመጣጣኝ፣ ትክክለኛ እና ኃላፊነት በሚሰማው ውይይት ብቻ ነው” ብለዋል።
ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳቱ ዓመፅ ከቁጥጥር ውጭ ከሆነ ከፍተኛ አሳዛኝ ሁኔታ እንደሚከሰት አስጠንቅቀዋል።
“እጅግ ከፍተኛ መጠን ያለው አሳዛኝ ሁኔታ የመከሰት እድል ስላጋጠመ”፣ “ለተሳተፉት ወገኖች የዓመፅ ሽክርክሪት ወደማይጠገን ገደል ከማምራቱ በፊት ለማስቆም የሞራል ኃላፊነቱን እንዲወስዱ ከልብ ጥሪ አቀርባለሁ!”
ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ሊዮ ሰላምን ለመፈለግ አገሮች ወደ ውይይት እንዲመለሱ ጸልየዋል።
“ዲፕሎማሲ ሚናውን መልሶ እንዲያገኝ እና በፍትህ ላይ የተመሠረተ ሰላማዊ አብሮ መኖርን የሚናፍቁ ሕዝቦች መልካምነት እንዲስፋፋ” ብለዋል። “እናም ለሰላም መጸለያችንን እንቀጥል” ካሉ በኋላ ቅዱስነታቸው መልእክታቸውን አጠቃለዋል።
