ር.ሊ.ጳ ሊዮ የእግዚአብሔር ቃል፣ የዓለም የሥጋ ደዌ ቀን፣ የክርስቲያን አንድነት እሁድን አክብረዋል!
የዚህ ዝግጅት አቅራቢ መብራቱ ኃ/ጊዮርጊስ-ቫቲካን
ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ሊዮ 14ኛ እሁድ ዕለት በርካታ ጉልህ የሆኑ በዓላትን አክብረዋል፣ ከእነዚህም መካከል የእግዚአብሔር ቃል የሚከበርበትን እሁድ፣ የሥጋ ደዌ በሽተኞች ዓለም አቀፍ ቀን እና ለክርስቲያናዊ አንድነት የተደርገው የጸሎት ሳምንት መደምደሚያ ይገኙበታል።
ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳቱ በቅዱስ ጴጥሮስ አደባባይ ለመልአከ እግዚአብሕእር ጸሎት ለተሰበሰቡት ምዕመናን ባደረጉት ንግግር፣ “ይህ መደበኛው የሦስተኛው ሳምንት እሁድ፣ የእግዚአብሔር ቃል እሑድ ተብሎ ይጠራል” ሲሉ አስታውሰዋል።
“ንፍስኤር ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንችስኮስ ይህንን ያቋቋሙት በቤተክርስቲያኒቱ ውስጥ ስለ ቅዱሳን መጻሕፍት ጥልቅ እውቀት እና ለእግዚአብሔር ቃል፣ በሥርዓተ አምልኮ እና በማህበረሰቦቻችን ሕይወት ውስጥ የበለጠ ትኩረት ለመስጠት ነው” ሲሉ አብራርተዋል።
“በእምነት እና በፍቅር ለዚህ መሠረታዊ ተልእኮ ራሳቸውን ለሚሰጡ ሁሉ አመሰግናለሁ እና አበረታታለሁ” ብለዋል።
የዓለም የሥጋ ደዌ ቀን
በየዓመቱ እ.አ.አ ጥር 25 ቀን የሥጋ ደዌ ያለባቸውን ሰዎች ለማክበር፣ ስለ በሽታው ግንዛቤን ለማሳደግ እና ከሥጋ ደዌ ጋር የተያያዘ መገለል እና መድልዎ እንዲቆም ጥሪ ለማቅረብ በሚከበረው የዓለም የሥጋ ደዌ ቀን፣ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳቱ ለተጎዱ ግለሰቦች ያላቸውን ቅርበት ገልጸዋል እና የሚንከባከቧቸውን ሰዎች አበረታተዋል።
"በዚህ በሽታ ለተጠቁ ሁሉ ያለኝን ቅርበት እገልጻለሁ። የራውል ፎሌሮ የጣሊያን ወዳጆች ማህበርን እና ለሥጋ ደዌ ላሉባቸው ሰዎች ክብራቸውን ለመጠበቅ የሚሠሩትን ሁሉ አበረታታለሁ" ብለዋል።
ለክርስቲያን አንድነት የጸሎት ሳምንት
ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ሊዮ በዚህ ዓመት እ.አ.አ ከጥር 18 እስከ 25/2026 ባለው ጊዜ ውስጥ ለክርስቲያናዊ አንድነት የተደርገው የአንድ ሳምንት ጸሎት ትላንት እሁድ ጥር 17/2018 ዓ.ም መጠናቀቁን አስታውሰው "በመጠራታችሁ በአንድ ተስፋ እንደ ተጠራችሁ አንድ አካልና አንድ መንፈስ አለ" (ኤፌሶን 4፡4) በሚል መሪ ቃል ተከብሮ ማለፉን አስታውቀዋል።
በጥር 17/2018 ዓ.ም ከሰዓት በኋላ ከሌሎች የክርስቲያን ቤተ እምነቶች ተወካዮች ጋር በቅዱስ ጳውሎስ ባዚሊካ የማታ ጸሎት በማድረግ ዝግጅቱ እንደተጠናቀቀ የሚታወስ ሲሆን በሚዲያ ቻናሎች የሚከታተሉትን ጨምሮ ለሁሉም ተሳታፊዎች ምስጋናቸውን ገልጸዋል።
