ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ሊዮ፥ በአውስትራሊያ በተፈፀመው ጥቃት እጅግ ማዘናቸውን ገለጹ
ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ሊዮ አሥራ አራተኛ አውስትራሊያ ውስጥ ታኅሳስ 5/2018 ዓ. ም. በተፈጸመ ጥቃት በሞቱት 16 ሰዎች የተሰማቸውን ጥልቅ ሐዘን ገልጸዋል። ቅዱስነታቸው ሐዘናቸውን የገለጹት በቫቲካን የቅድስት መንበር ጽሕፈት ቤት በኩል ለሲድኒ ከተማ ሊቀ ጳጳስ አቡነ አንቶኒ ፊሸር በተላኩት የቴሌግራም መልዕክት ላይ እንደሆነ ታውቋል።
የዚህ ዝግጅት አቅራቢ ዮሐንስ መኰንን - ቫቲካን
ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ሊዮ አሥራ አራተኛ በአውስትራሊያ ቦንዲ የባሕር ዳርቻ ስለተፈጸመው ጥቃት ከሰሙ በኋላ የጻፉትን የቴሌግራም መልዕክት ለሲድኒ ከተማ ሊቀ ጳጳስ አቡነ አንቶኒ ፊሸር የላኩት በቅድስት መንበር ዋና ጸሐፊ ብጹዕ ካርዲናል ፒዬትሮ ፓሮሊን ናቸው።
ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ሊዮ አሥራ አራተኛ በአውስትራሊያ ቦንዲ የባሕር ዳርቻ ለ “ሃኑካህ” በዓል የተሰበሰቡት የአይሁድ ማኅበረሰብ አባላት ሕይወታቸውን በማጣታቸው የተሰማቸውን ጥልቅ ሐዘን ገልጸዋል። ቅዱስነታቸው በመልዕክታቸው፥ “በዚህ ትርጉም የለሽ የዓመፅ ድርጊት ለተጎዱት በሙሉ ያለኝን መንፈሳዊ ቅርበት አረጋግጣለሁ” ሲሉ አክለዋል።
ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ሊዮ አሥራ አራተኛ፥ “በዓመፅ የተፈተኑት ሰዎች ንስሐ ገብተው የሰላም መንገድን እንደሚፈልጉ ያላቸውን ተስፋ ገልጸዋል። ከአደጋው በማገገም ላይ ለሚገኙት እና የሚወዷቸውን ሰዎች በሞት ላጡት በሙሉ መጽናናትን ተመኝተውላቸዋል።
ቅዱስነታቸው በቴሌግራም የሐዘን መልዕክታቸው ለሁሉም አውስትራሊያውያን የሰላም እና የጥንካሬ መለኮታዊ በረከትን በመለመን የሞቱትን ሰዎች ነፍስ ለእግዚአብሔር በአደራ አቅርበዋል።
16 Dec 2025, 12:08
