“አምነስቲ ኢንተርናሽናል” የጋና ባለሥልጣናት የፀረ-ጠንቋይ ክሶች ረቂቅ ሕግን እንዲያፀድቁ አሳሰበ
የዚህ ዝግጅት አቅራቢ ዮሐንስ መኰንን - ቫቲካን
“አምነስቲ ኢንተርናሽናል” የጋና ባለሥልጣናት “ጥንቋይ” ተብሎ ፍትሃዊ ባልሆነ መንገድ ለተከሰሱ በመቶዎች ለሚቆጠሩ ተጎጂዎች የሚደረግላቸውን ጥበቃ ማዘግየት እንደሌለባቸው ተናግሯል።
በሕይወት የመኖር መብት
“እንደ ጎርጎሮሳውያኑ ሐምሌ 23/2020 ዓ. ም. ጠንቋይ ናት ተብላ የተከሰሰችው የ90 ዓመቷ አኳ ዴንቴህ በሰሜን ጋና በሚገኘው ሳቫና ክልል ካፋባ በተባለችው የትውልድ መንደሯ በሕዝብ ፊት መገደሏ ይታወሳል።
“አኳን ሲደበድቧት በቪዲዮ ምስል የታዩት ሁለት ሴቶች እንደ ጎርጎሮሳውያኑ 2023 ዓ. ም. በግድያ ወንጀል ተከስሰው 12 ዓመት ተፈርዶባቸዋል። በጥንቆላ የተከሰሱ በመቶዎች የሚቆጠሩ ሌሎች ሴቶች ለሕይወታቸው በመፍራት ከማኅበረሰባቸው ለመሸሽ ተገደዋል” ሲሉ የ “አምነስቲ ኢንተርናሽናል” ባለሥልጣን ተናግረዋል።
በጋና ውስጥ የሚገኙ አንዳንድ አጋር ድርጅቶችን የጠቀሰው “አምነስቲ ኢንተርናሽናል”፥ የአኳ ጉዳይ የጥንቆላ ክሶች አስከፊ መዘዝ ከሚያስከትሉ እና ልብ ከሚሰብሩ ምሳሌዎች መካከል አንዱ እንደሆነ ተናግሯል። በጋና የሚገኙ የመብት ተሟጋቾች እና በጎ አሳቢ ዜጎች ክሶቹ የአንድን ሰው የመኖር፣ የደህንነት እና ያለመድልዎ የመኖር መብትን የሚጥሱ በመሆናቸው ክሶቹን ወንጀል ማድረግ ያስፈልጋል” ሲሉ አስረድተዋል።
ስቃይ እና ዓመፅ
የጥንቆላ ክሶች ብዙውን ጊዜ የሚጀምሩት በቤተሰብ ውስጥ ወይም በማኅበረሰብ አባላት መካከል ሲሆን እንደ ሕመም ወይም ሞት ባሉ አሳዛኝ ክስተቶች በኋላ እንደሆነ ታውቋል። በድህነት የሚኖሩ፣ የጤና እክል ወይም የአካል ጉዳተኛ የሆኑ አረጋውያን ሴቶች የመከሰስ እድላቸው ከፍተኛ ሲሆን፥ በተመሳሳይ ሁኔታ ተጋላጭ የሚሆኑት ሴቶች ከመደበኛ ሚናቸው ጋር የማይጣጣሙ እንደሆኑ ተገልጿል። በጥንቆላ ላይ ያለው እምነት በዓለም አቀፍ ሕግ የተጠበቀ ቢሆንም ከእምነቱ ለሚመጡ ጎጂ ልማዶች ጥበቃ እና ካሳ እንደሚያስፈልጋቸው ተገልጿል።
“አምነስቲ ኢንተርናሽናል” የጋና ፓርላማ የፀረ-ጠንቋይ ክሶችን ረቂቅ ሕግ እንደ ጎርጎሮሳውያኑ በሐምሌ ወር 2023 ዓ. ም. እንዳፀደቀው ተናግሯል። ረቂቅ ሕጉ ግለሰቦችን በጥንቆላ መክሰስ፣ ለተከሰሱ ሰዎች የመከላከያ እርምጃዎችን እና የድጋፍ ሥርዓቶችን ማቋቋም እና ተጎጂዎች ፍትህ እና ካሳ እንዲፈልጉ ግልጽ የሆነ የሕግ መንገድን ማቅረብ ሕገ-ወጥ ለማድረግ ሞክሯል” ብሎ ሕገ-መንግሥታዊ ጉዳዮችን በመጥቀስ በቀድሞው ፕሬዝዳንት ናና አኩፎ-አዶ እንዳልተፈረመ ገልጾ፥ ምክንያቱም በመንግሥት ባለቤትነት የተያዘው ረቂቅ ሕግ ሳይሆን የግል አባል ረቂቅ ሕግ ሆኖ በመቅረቡ እና ከዚያን ጊዜ ጀምሮ ምንም ዓይነት ረቂቅ ሕግ ለፓርላማ አለመቅረቡ አስረድቷል።
ሁሉን አቀፍ አቀራረብ
የመብት ቡድኑ የጋና ማኅበረሰብ የክሶቹን ዋና ዋና ምክንያቶች በጥልቀት እንዲመረምር አሳስቦ፥ ወደ ክሶቹ የሚያመሩ ጉዳዮችን በጥልቀት የሚፈታ የበለጠ ሁሉን አቀፍ አቀራረብን እንደሚያበረታታ ታውቋል።
“የጥንቆላ ክሶችን ወንጀለኛ ማድረግ ብቻውን ችግሩን አይፈታውም” ያለው የመብት ቡድኑ፥ አንዳንድ የግንዛቤ ማስጨበጫ ተነሳሽነቶች መንግሥታዊ ባልሆኑ ድርጅቶች እና በክልል መንግሥት ደረጃ ቢካሄዱም ከጥንቆላ ክሶች ጋር የተያያዙ አመለካከቶችን ሙሉ በሙሉ ለመዋጋት በቂ አይደሉም” ሲል አሳስቧል።