የኡጋንዳ ሰማዕታት ቀን በሮም ተከበረ
አቅራቢ ዘላለም ኃይሉ ፥ አዲስ አበባ
በዕለቱ በደማቅ ሁኔታ በተደረገው መስዋዕተ ቅዳሴ ላይ በርካታ የኡጋንዳ ካህናት እንዲሁም ሮም ውስጥ ትምህርታቸውን እየተከታተሉ የሚገኙ እና በሥራ ላይ ያሉ ገዳማዊያትን ጨምሮ በጣሊያን የሚገኙ የተለያዩ የአፍሪካ ኤምባሲዎች ተወካዮች፣ መቀመጫቸውን ሮም ያደረጉ የቅድስት መንበር እና የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ኤጀንሲዎች ተወካዮች ተገኝተዋል።
ሃይማኖት እና የጸና እምነት
ብፁዕ ካርዲናል ቱርክሰን በመስዋዕተ ቅዳሴው ወቅት ባሰሙት ቃለ ምዕዳን ምዕመናን የኡጋንዳ ሰማዕታት ለሃይማኖታቸው ሲሉ ሁሉንም ነገር እንዲሠዉ ያነሳሳቸውን ጽኑ እምነት ተምሳሌት በማድረግ ህይወታቸውን በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ላይ እንዲመሰርቱ ያሳሰቡ ሲሆን፥ በመጽሃፍ ቅዱስ ውስጥ በ1ኛ መጽሐፈ መቃብያን ላይ የማይናወጥ ድፍረት እና እምነት ስላላቸው ስለ ሦስቱ ወንድማማቾች ታሪክ በመጥቀስ፥ በመጽሃፉ ውስጥ የተገለጹት እነዚህ ወንድማማቾች ንጉሱ የጠየቃቸውን ጥያቄዎች ለመቀበል ፈቃደኞች ባለመሆን ማንነታቸውን እና ባህላቸውን እስከ ሞት ድረስ መጠበቃቸውን አስረድተዋል።
ለጥሪ ቁርጠኛ መሆን
የቫቲካኑ ሃይማኖታዊ መሪ አክለውም ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ዛሬ በሁሉም ምዕመናን ህይወት ውስጥ እንደሚኖር አጽንዖት ሰጥተው በመግለጽ፥ ሁሉም የክርስቶስ ተከታዮች የሰማዕታቱን የማይናወጥ ቁርጠኝነት እንዲያንጸባርቁ መጠራታቸውን አስታውሰዋል።
ብፁዕ ካርዲናል ቱርክሰን በመጨረሻም የኡጋንዳ ሰማዕታት ታሪክ ሁሉም የተጠመቁ ሰዎች ለእምነታቸው፣ ለትዳር አጋራቸው እንዲሁም ለሃይማኖታዊ ጥሪያቸው ቁርጠኛ እና ዝግጁ እንዲሆኑ ጥሩ ማሳያ ነው በማለት አጠቃለዋል።