በፊሊፒንስ “የናዝሬቱ ኢየሱስ” በዓል የሚያከብሩ ምዕመናን ቁጥር እጅግ ከፍተኛ እንደሆነ ተነገረ
የዚህ ዝግጅት አቅራቢ ዮሐንስ መኰንን - ቫቲካን
ከታኅሳስ 22 እስከ ጥር 2/2018 ዓ. ም. ባለው ጊዜ ውስጥ “የናዝሬቱ ኢየሱስ” በዓልን ለማክበር 10 ሚሊዮን የሚጠጉ ሰዎች ወደ ፊሊፒንስ መዲና ማኒላ እንደሚጓዙ ታውቋል።
ይህ ሃይማኖታዊ ፌስቲቫል ሁለት ዋና ዋና ክፍሎች ያሉት ሲሆን፥ የመጀመሪያው የዘጠኝ ቀናት ጸሎት “ኖቬና” እና “Traslacion” ወይም “ዑደት” በመባል የሚታወቅ የአገሪቱ ትልቁ እና ረጅሙ ዓመታዊ ዑደት መሆኑ ተመግሯል።
ይህን በዓል ለማክበር በዋና ከተማዋ ማኒላ ጎዳናዎች ላይ መስቀልን የተሸከመ የኢየሱስ ክርስቶስ ግዙፍ የእንጨት ሐውልት ዑደት የሚያደርግ ሲሆን በዚህ ዓመት ለ31 ሰዓታት የቆየ ትልቅ እና ረጅም ዑደት መካሄዱን መንግሥት መዝግቧል።
ተንቀሳቃሽ የኢየሱስ ክርስቶስ ግዙፍ የእንጨት ሐውልት
በ17ኛው ክፍለ ዘመን የተጀመረው እና በእሳት ቃጠሎ የጠቆረውን የኢየሱስ ክርስቶስ የእንጨት ሐውልት እንደ ጎርጎሮሳውያኑ በ1606 ዓ. ም. ከሜክሲኮ ወደ ፊሊፒንስ ማኒላ ያመጡት የቅዱስ አጎስጢኖስ ማኅበር ሚስዮናውያን እንደ ነበሩ ይነገራል።
የፊሊፒንስ ካቶሊክ ማኅበረሰብ “የናዝሬቱ ኢየሱስ” የእንጨት ሐውልት ወደ አገሪቱ የገባበትን 400ኛ ዓመት እንደ ጎርጎሮሳውያኑ በ2006 ዓ. ም. ያከበሩ ሲሆን ሐውልቱ በአሁኑ ጊዜ በኪያፖ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ እንደሚገኝ ይህ ትንሹ ባዚሊካ “የናዝሬቱ ኢየሱስ” ቤተ መቅደስ በመባል ይታወቃል።
ክብረ በዓሉ በእስያ ውስጥ እጅግ ከሚወደዱ ሃይማኖታዊ በዓላት መካከል አንዱ ሲሆን እስከ ዛሬ ድረስ በዘጠኝ ቀናቱ የጸሎት እና የዑደት ሥነ-ሥርዓቶች ላይ የተገኙት ምዕመናን ቁጥር ወደ 9,640,290 መድረሱ ተዘግቧል።
በሀገሪቱ ውስጥ ከሚገኙት ሰፊ የመሰብሰቢያ ሥፍራዎች መካከል አንዱ ከሆነው ከኪሪኖ ግራንድስታንድ የሚጀምረው የኢየሱስ ክርስቶስ ሐውልት ዑደት የኪያፖ አውራጃን የሚያቋርጥ ሲሆን ዑደቱ ሐውልቱ እንደ ጎርጎሮሳውያኑ በ1787 ዓ. ም. ወደ ኪያፖ ቤተ ክርስቲያን መዛወሩን የሚያስታውስ መሆኑ ታውቋል።
መንፈሳዊ ነጋዲያኑ ሰባት ኪሎ ሜትር ያኅል በባዶ እግራቸው የሚጓዙ ሲሆን በሐውልቱ ላይ ካሉ ልብሶች ጋር እንዲመሳሰል ሲባል ነጋዲያኑ ቀይ ቀለም ያላቸውን ልብሶች እንደሚለብሱ ታውቋል። በዑደቱ ወቅት ምእመናኑ ገመዶችን ለመንካት ወይም ሐውልቱን በተሸከመው ሠረገላ ላይ ለመውጣት ሲጥሩ ታይተዋል።