ፈልግ

ከምሥራቅ አገራት የደረሱን ዜናዎች - መስከረም 14/2018 ዓ. ም.

በዚህ ሳምንት ከምሥራቅ አብያተ ክርስቲያናት ከደረሱን ዜናዎች መካከል፥ የሶርያ ሕጻናት በአመጽ መካከል የተስፋ ምልክት ሆነው መጠመቃቸውን፣ የኢየሩሳሌም የላቲን ፓትርያርክ የቤተሰቦችን የትምህርት ቤት ዕዳ መሠረዛቸውን እና ኢራቅ አዲስ የቅድስት መንበር ሐዋርያዊ እንደራሴ ማግኘቷን የሚገልጹ ዜናዎች ይገኙባቸዋል።

የዚህ ዝግጅት አቅራቢ ዮሐንስ መኰንን - ቫቲካን

በማር ኤልያስ የ22 ሕጻናት ጥምቀት

በደማስቆ ዱኢሌህ ሠፈር በሚገኘው የግሪክ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ማር ኤልያስ ላይ ​​ጥቃት ከተፈጸመ ከሦስት ወራት በኋላ 22 የሶርያ ሕጻናት ለሰማዕታቱ ክብር ሲሉ የተስፋ ምልክት በመሆን የጥምቀት ምስጢር ተቀብለዋል።

አባ ዩሃና ሻሃዳ፥ ይህ ምልክት የምእመናን እምነት ፈተና ቢደርስበትም ሕይወትን እና ተስፋን ለልጆቻቸው ለማስተላለፍ ያላቸውን ፍላጎት የሚያረጋግጥ መሆኑን አስታውሰዋል።

አባ ዩሃና ሻሃዳ፥ ማኅበረሰባቸው በሕይወት ለመቆየት ስላለው ሥር የሰደደ ቁርጠኝነት አጽንኦት በመስጠት፥ “ልጆቻችንን ማጥመቃችንን፣ ማስተማራችንን እና በዚህች ቤተ ክርስቲያን እና በዚህች ምድር ማሳደግን እንቀጥላለን” በማለት አክለዋል።

በቅድስት ሀገር የትምህርት ቤት ዕዳ መሰረዝ

የኢየሩሳሌም የላቲን ፓትርያርክ ብጹዕ ካርዲናል ፒየርባቲስታ ፒዛባላ እንደ ጎርጎሮሳውያኑ ከ2024–2025 ዓ. ም. የትምህርት ዘመን በፊት በቅድስት ሀገር በሚገኙ የካቶሊክ ትምህርት ቤቶች በተማሪዎች ቤተሰቦች ላይ የተከማቸው የትምህርት ቤት ዕዳ መሠረዙን አስታውቀዋል።

ለዚህም ልዩ ምክንያት ሆኖ የቀረበው፥ ብዙዎች በጋዛ ጦርነት የተጎዱ እና የቱሪዝም ገቢ የተነፈጉ ቤተሰቦች የልጆቻቸውን የትምህርት ቤት ወጭዎች መሸፈን በማይችሉበት ደረጃ ላይ በመድረሳቸው ተብሏል።

ብጹዕ ካርዲናል ፒየርባቲስታ በመልዕክታቸው ላይ እንደገለጹት፥ እንዲህ ዓይነቱ ውሳኔ ከባድ መሆኑን አምነው፣ ዋጋውን ከግምት ውስጥ በማስገባት ውሳኔው “አስፈላጊ ነው!” ሲሉ አስረድተዋል።

ይህ ውሳኔ እንደ ጎርጎሮሳውያን ከ2025 ዓ. ም. የተስፋ ኢዮቤልዩ መንፈስ ጋር የተገናኘ ተጨባጭ የአብሮነት መግለጫ እንደሆነ እና የውስጥ ለውጥ ብቻ ሳይሆን ፍትህን፣ ትክክለኛነትን እና መደጋገፍን የሚያጎለብት እንደሆነ ገልጸዋል።

በኢራቅ አዲስ ሐዋርያዊ እንደራሴ መሾም

ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ሊዮ አሥራ አራተኛ፥ ሊቀ ጳጳስ አቡነ ሚሮስላው ዋቾውስኪን በኢራቅ የቅድስት መንበር ሐዋርያዊ እንደራሴ አድርገው ሾመዋቸዋል። የ55 ዓመቱ ፖላንዳዊ ዲፕሎማት በአሁኑ ወቅት በቅድስት መንበር የመንግሥታት እና ዓለም አቀፍ ድርጅቶች ግንኙነት ጽሕፈት ቤት ምክትል ዋና ጸሃፊ ናቸው።

የክኅነት ማዕረጋቸውን እንደ ጎርጎሮሳውያኑ በ1996 ዓ. ም. የተቀበሉት ሊቀ ጳጳስ አቡነ ሚሮስላው፥ የሕግ-ቀኖና ትምህርት የተከታተሉ እና ሌሎች ከፍተኛ መንፈሳዊ ትምህርቶችንም በጳጳሳዊ አካዳሚ የተከታተሉ ሲሆን፥ ወደ ቅድስት መንበር ዲፕሎማሲያዊ አገልግሎት የገቡት እንደ ጎርጎሮሳውያኑ በ2004 ዓ. ም. መሆኑ ይታወሳል።

ዲፕሎማሲያዊ አገልግሎታቸውን በሴኔጋል፣ በቪየና የተባበሩት መንግሥታት ዓለም አቀፍ የአቶሚክ ኢነርጂ ኤጀንሲ፣ በአውሮፓ የደህንነት እና ትብብር ድርጅት እንዲሁም በፖላንድ ማበርከታቸው ተገልጿል።

ወደ ባግዳድ የተላኩት ለኪንሻሳ የተሾሙትን ሊቀ ጳጳስ ሚትጃ ሌስኮቫርን ተክተው መሆኑ ተነግሯል።

 

 

25 Sep 2025, 16:14